ኢትዮጵያዊው የመሃል ተከላካይ ዋሊድ አታ ለስዊድኑ ኦስተርሰንድስ ኤፍኬ ለመጫወት ፊርማውን አኑሯል፡፡ ተጫዋቹ ለሶከር ኢትዮጵያ እንዳረጋገጠው ከሆነ ለአንድ ዓመት በሚቆይ ውል ነው ለኦስተርሰንድስ ለመጫወት የተስማማው፡፡
የስዊድንን ሊግ በ2009 ከኤአይኬ ጋር ማሸነፍ የቻለው የ29 አመቱ ዋሊድ የህክምና ምርመራውን በተሳካ ሁኔታ አጠናቅቋል፡፡ የመጀመሪያ ልምምዱንም ትላንት ከአዲሱ ክለቡ ጋር አድርጓል፡፡
ዋሊድ ከቱርኩ ክለብ ገንሰልበርሊጊን ጋር ነበረውን የሶስት ዓመት ውል በጥር ወር በስምምነት ካፈረሰ በኃላ አዲስ ክለብ ሲፈልግ የቆየ ሲሆን በስዊድን ሊግ የሚወዳደሩ ሶስት ክለቦች ተጫዋቹን ለማስፈረም ፍላጎታቸው አሳይተው ነበር፡፡ ኤልፍስበርግ፣ ብሮንድባይ እና ጎተንበርግ የዋሊድ ፈላጊዎች ነበሩ፡፡ በተለይ ኤልፍስበርግ ወደ ዳይናሞ ሞስኮ ለመዛወር ከጫፍ የደረሰውን ሰባስቲያን ሆልመን ምትክ አድርጓ ዋሊድን ማስፈረም ፈልጎ ነበር፡፡
በግርሃም ፖተር የሚሰለጥነው ኦስተርሰንድስ በ1996 የተመሰረተ ሲሆን በ2015 የውድድር ዘመን ከሁለተኛ ዲቪዝዮን ወደ ዋናው ሊግ ማደግ ችሏል፡፡
ዋሊድ በግል የኢንስተግራም ገፁ ላይ ለኦስተርሰንድስ መፈረሙ እንዳስደሰተው ተናግሯል፡፡
ያጋሩ