​ኮንፌዴሬሽን ካፕ | በዛሬው ጨዋታ ጉዳት ያስተናገዱት ሁለቱ ተጫዋቾች ወቅታዊ ሁኔታ

የኮንፌዴሬሽን ካፕ የቅድመ ማጣሪያ የመልስ ጨዋታ በዛሬው ዕለት በአዲስ አበባ ስታዲየም ሲከናወን በሁለተኛው አጋማሽ ከፍተኛ ጉዳት ያስተናገዱት ሁለቱ ተጫዋቾች በምን ሁኔታ ላይ ይገኛል። 

በሁለተኛው አጋማሽ 76ኛው ደቂቃ የቅጣት ምት ያገኙት ሞናስቲሮች አጋጣሚውን ወደ ጎልነት ለመቀየር ሲጥሩ ፋሂም ቤን ረመዳን 

እና ሚኬል ሳማኬ በአስደንጋጭ  ሁኔታ ተጋጭተው ጉዳት አስተናግደዋል። የዩ ኤስ ሞናስተር ተጫዋች ፋሂም ቤን ረመዳን ምላሱ ተንሸራቶ የመተንፈሻ አካሉን ሲዘጋው በአንደኛው የጆሮው ክፍል ደም የፈሰሰው ሲሆን የፋሲሉ ግብ ጠባቂ ሚኬል ሳማኪ ደግሞ ጭንቅላቱ ላይ መጠነኛ መፈንከት አጋጥሞታል። 

ይህን ተከትሎ ከሜዳው ውጭ ይገኙ የነበሩትን ተመልካች እና በሜዳ ላይ የነበሩትን የሁለቱን ቡድኖች አባላትን በተከሰተው ከባድ ጉዳት ተደናግጠው ሲያለቅሱ እና ሲጨነቁ እንደነበረ የተስተዋለ ሲሆን በሁለት አንቡላንስ ተጭነው ለህክምና በስታዲየሙ አቅራቢያ ወደሚገኘው ቤተ ዛታ ሆስፒታል እንዲያመሩ ተደርጓል። 

በአሁኑ ሰዓት ሁለቱም ተጫዋቾች የተሻለ ህክምና አግኝተው በጥሩ ሁኔታ እንደሚገኙ ከጨዋታው መጠናቀቅ በኃላ በስፍራው በማቅናት ለማረጋገጥ ችለናል።

© ሶከር ኢትዮጵያ