የቤትኪንግ የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ሁለተኛ ሳምንት ቁጥሮች እና ዕውነታዎች

ከዓርብ እስከ እሁድ በተደረጉት የሁለተኛ ሳምንት ቤትኪንግ የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ጨዋታዎች ላይ የተመዘገቡ ቁጥራዊ መረጃዎች እና ዕውነታዎችን እንደሚከተለው አጠናቅረናል።

– በዚህ ሳምንት በተካሄዱ ስድስት ጨዋታዎች 15 ጎሎች (በጨዋታ በአማካይ 2.5 ጎሎች በጨዋታ) ተቆጥረዋል። ይህም ከባለፈው ሳምንት በሁለት ጎሎች ያነሰ ነው።

– ከ15 ጎሎች መካከል 9 ኳሶች ከክፍት የጨዋታ እንቅስቃሴ ሲቆጠሩ 2 ኳሶች ከቆመ ኳስ መነሻነት ተቆጥረዋል። አራት ጎሎች ደግሞ በፍፁም ቅጣት ምት ተቆጥረዋል።

– ከአስራ አምስቱ ጎሎች ከአንዱ በቀር ሳጥን ውስጥ ተመትተው ወደ ጎልነት የተቀየሩ ሲሆኑ ፉአድ ፈረጃ ብቻ ከሳጥን ውጪ መትቶ አስቆጥሯል።

– ጎሎች ከተቆጠሩበት መንገድ ጋር በተያያዘ ከ15 ጎሎች መካከል እንባለፈው ሳምንት ሁሉ በዚህ ሳምንትም አንድ ጎል ብቻ (መስፍን ታፈሰ) በጭንቅላቱ ገጭቶ ሲያስቆጥር ሌሎቹ ጎሎች በእግር ተመተው የተቆጠሩ ናቸው።

– በሳምንቱ የተቆጠሩት 15 ጎሎች በ14 የተለያዩ ተጫዋቾች የተቆጠሩ ሲሆን የድቻው ስንታየሁ መንግሥቱ ሁለት ጎሎች አስቆጠሮ ቀሪዎቹ ተጫዋቾች አንድ አንድ አስቆጥረዋል።

– የዚህ ሳምንት ዲሲፕሊን ሪከርድን ስንመለከት በስድስት ጨዋታዎች 20 የማስጠንቀቂያ ካርዶች እና ሦስት ቀይ ካርዶች ተመዘዋል። ይህም ከባለፈው ሳምንት በሦስት ቢጫ እና በሁለት ቀይ ብልጫ አሳይቷል።

– ቡና እና ሆሳዕና በሦስት ቢጫ እና አንድ ቀይ በርካታ ካርድ የተመዘዘባቸው የሳምንቱ ቡድን ሆኗል።

– ባለፈው ሳምንት የማስጠንቀቂያ ያልተመዘገበበት ሰበታ ከተማ በዚህ ሳምንት ምንም ካርድ ያልተመለከቱ ቡድን ሆኗል።

ዕውነታዎች

– ያለፈው ዓመት ውድድር ሙሉ ለሙሉ መሰረዙን ታሴቢ ካደረግን ሀዲያ ሆሳዕና በፕሪምየር ሊግ ታሪኩ ለመጀመርያ ጊዜ ሁለት ተከታታይ ጨዋታ አሸንፏል። ቡድኑ ለመጀመርያ ጊዜ በተሳተፈበት የ2008 ፕሪምየር ሊግ ሙሉውን የውድድር ዓመት አንድ ጨዋታ ብቻ ነበር ያሸነፈው።

– ሙሉጌታ ምህረት በክለብ ዋና አሰልጣኝነት ሀዋሳ ከተማን እየመራ የመጀመርያ ጨዋታውን አድርጓል። የቀድሞው ተጫዋች ክለቡን በአምበልነት እየመራ ሁለት ጊዜ የሊጉን ዋንጫ ያነሳ ሲሆን በአሰልጣኝነትም ይህን ታሪክ የመድገም ጉዞውን ዓርብ ከሰበታ ከተማ ጋር አድርጎ በሽንፈት ጀምሯል።

– ተመስገን ካስትሮ ለሁለት ዓመት ከተጠጋ ጊዜ በኋላ ለመጀመርያ ጊዜ በቀዳሚ ተሰላፊነት ጨዋታ ጀምሯል። ሁለገቡ ተጫዋች ከጥር 19 ቀን 2011 በኋላ ባደረገው ጨዋታ ለአርባ ስድስት ደቂቃዎች ሜዳ ላይ ቆይቶ በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል።


© ሶከር ኢትዮጵያ