የ45 ዓመቱ ጂያኒ ኢንፋንቶኖ የአለማቀፉ እግርኳስ አስተዳዳሪ አካል ፊፋ ፕሬዝደንት ሆነው ዛሬ ዙሪክ ላይ በተደረገ ምርጫ አሸንፈው ተመርጠዋል፡፡
በሁለት ዙር በተደረገው ምርጫ የባህሬኑ ሼክ ሳልማን ከሌሎች ተወዳዳሪዎች በተሻለ የኢንፋንቲኖ ዋነኛ ተቀናቃኝ ሆነው ቀርበው ነበር፡፡ ሳልማን እና ኢንፋንቲኖ በመጀመሪያው ዙር ተቀራራቢ ድምፅ በማግኘታቸው ውድድሩ ከሞላ ጎደል በሁለቱ ሰዎች መካከል ሆኖ ነበር፡፡
በምርጫው ላይ ኢትዮጵያ የድምፅ አሰጣጡን ለመታዘብ እና የድምፅ ቆጠራውን ለማካሄድ ከተመረጡ ሃገራት መካከል የነበረች ሲሆን የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌድሬሽን ፕሬዝደንት ጁነይዲ ባሻ በደምፅ አሰጣጡን በመታዘብ እና በቆጠራው ላይ ተሳትፈዋል፡፡
የአፍሪካ እግርኳስ ኮንፌድሬሽን (ካፍ) አብዛኞቹ አባል ሃገራት ድምፃቸውን ለሼክ ሳልማን ቢሰጡም ባህሬናዊውን ከመሸነፍ ሊያድኑ አልቻሉም፡፡
የአውሮፓ እግርኳስ ማህበር ዋና ፀሃፊ የነበሩትና የስዊዘርላንድ እና ጣሊያን ጥምር ዜግነት ያላቸው ኢንፋንቲኖ የአለም ዋንጫን ወደ 40 ተሳታፊ ሃገራት ለማሳደግ እና የአፍሪካ ሃገራት በአለም ዋንጫ ያላቸውን የተሳትፎ ቁጥር ለማሳደግ እንደሚፈልጉ መግለፃቸው ይታወሳል፡፡
የኢ.እ.ፌ. ፕሬዝደንት ጁነዲ ባሻ በግል የትዊተር ገፃቸው ለኢንፋንቲኖ የእንኳን ደስ አለህ መልክት ልከዋል፡፡