ከፍተኛ ሊግ | ፌደራል ፖሊስ ሊጉን በድል ጀምሯል

ባቱ ላይ በተደረገው የምድብ ሀ ጨዋታ ፌደራል ፖሊስ ወሎ ኮምቦልቻን አሸንፏል።

በመጀመሪያው አጋማሽ ቀዝቀዝ ባለ ፉክክር የተጀመረው የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ ሙከራዎች በቶሎ አልታዩበትም። 8ኛው ደቂቃ ላይ የፌደራል ፖሊሱ አንተነህ ተሻገር ከቅጣት ምት ካደረገው ሙከራ ሌላ ኳስ ተቆጣጥረው በመጫወት የተሻሉት ወሎ ኮምቦልቻዎች ወደ ተጋጣሚ የግብ ክልል ለመድረስ የሚደርጉት ጥረት ስኬታማ ሳይሆን ቢቀረም በ20ኛው ደቂቃ ላይ አብይ ቡልቲ በግንባሩ ዘሎ በመግጨት የኦሜድላን ግብ ለመፈተሽ ሞክሯል። 38ኛው ደቂቃ ላይም እንዳለማው ታደሰ ሦስት ተጫዋቾችን በማለፍ የሞከረው ሙከራ ኢላማውን ጠብቆ ነበር።

ኦሜድላዎች ከርቀት በሚሻገሩ ኳሶች ተፅዕኖ ለመፍጠር ያደረጉት ጥረት ፍሬ ባያፈራም በተጋጣሚያቸው የሜዳ ክፍል ላይ ኳስን ከሁለቱ መስመሮች በማሻገር ጫና ለመፍጠር ጥረዋል። በ30ኛው ደቂቃም ብሩክ ብርሃኑ ፍፁም ቅጣት ምት የተከለከለበት ምክንያት ሊሰጠን ይገባል በሚል የቴክኒካል ክስ አስይዘዋል።

ሁለተኛው አጋማሽ ሲጀምር እጅግ ብልጫን ወስደው መጫወት በቻሉት ፌደራሎች በኩል 47ኛው ደቂቃ ላይ አስቻለው መሀመድ ከመስመር ቻላቸው ቤዛ ያሻማውን ኳስ ወደግብነት ለውጦታል። ከግቡ መቋጠር በኋላ ሙሉ ለሙሉ በሚባል መልኩ ወደ መከልከሉ ያዘነበሉት ኦሜድላዎች የተጋጣሚያቸውን የኳስ ፍሰት በማቋረጥ ተጠምደዋል።

በወሎዎች በኩል 60ኛው ደቂቃ ላይ ተመስገን ታሪኩ ያሻገረውን ኳስ አስቻለው ማህመድ አፈትልኳ በመውጣት ያገኘውን አጋጣሚ ሳይጠቀምበት ቀርቷል። ቡድኑ ደቂቃ እየገፋ በመጣ ቁጥር መረጋጋት ተስኖት ወደፊት የሚጣሉ ኳሶችም ውጤት ሳያስገኙ ቀርተዋል። በዳንኤል ዘለቀ እና እንዳለማው ታደሰ የተደረጉ መከራዎችም ወደ ግብነት ሳይለወጡ ጨዋታው ተጠናቋል።


© ሶከር ኢትዮጵያ