ፕሪምየር ሊግ | የቅጣት ውሳኔዎች ሲተላለፉ የረቡዕ ጨዋታዎች ላይ የሰዓት ቅያሪ ተደርጓል

በቤትኪንግ የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ሁለት ጨዋታዎች ሰዓት ላይ ቅያሪ ሲደረግ የዲሲፕሊን ቅጣት ውሳኔዎች ተላልፈዋል።
የሊጉ የስምንተኛ ሳምንት ጨዋታዎች ነገ የሚጀምሩ ሲሆን የሊጉ አወዳዳሪ አካል ባሳለፈው ውሳኔ መሰረት ረቡዕ የሚደረጉ ጨዋታዎች የሚካሄድባቸው ሰዓቶች ላይ ቅይይር ተደርጓል። በዚህም መሠረት 9:00 እንዲደረግ መርሐ ግብር ወጥቶለት የነበረው የሀዋሳ ከተማ ከ ሲዳማ ቡና ጨዋታ ወደ 4:00 ሲመጣ፤ 4:00 የነበረው የፋሲል ከነማ እና አዳማ ከተማ ጨዋታ ወደ 9:00 ተቀይሯል።

ለለውጡ ምክንያት የሆነው “የአንድ ቡድን ሁለት ተከታታይ ጨዋታዎች የሚወጣው ፕሮግራም ከ72 ስዓት ማነስ የለበትም የሚለውን የውድድር ደንብ ለማክበር ሲባል” መሆኑ ተገልጿል።

በተያያዘ 7ኛ ሳምንት ጨዋታዎች በተከሰቱ ግድፈቶች ላይ የሚከተሉት ውሳኔዎች ተላልፈዋል።

– ጅማ አባጅፋር አርብ ጥር 7 ከቅዱስ ጊዮርጊስ ያደረገው ጨዋታ 5 ደቂቃ ዘግይቶ አንዲጀመር ምክኒያት ስለመሆኑ ከጨዋታ ታዛቢ ሪፖርት ቀርቦበታል ። ክለቡ ለፈፀመው ጥፋት በኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ደንብ መሰረት 15,000 ቅጣት እንዲከፍል፤ በተጨማሪም ጨዋታውን በብሮድካስት የሚያስተላልፈው ድርጅት ሼር ካምፓኒው ላይ የሚያስተላልፈው የገንዘብ ቅጣት ካለ ክለቡ ወጪውን ሙሉ በሙሉ እንዲከፍል ወስኗል።

2. ታከለ ጨቅሌ (የባህርዳር ከተማ ቡድን መሪ) ቅዳሜ ጥር 8 ክለቡ ከሀዋሳ ከተማ ጋር ያደረገው ጨዋታ ካለቀ በኋላ የዕለቱን አራተኛ ዳኛ አፀያፊ ስድብ መሳደቡና ለድብድብ መጋበዙ ከዋና ዳኛውና ከጨዋታ ታዛቢ ሪፖርት ቀርቦበታል። የቡድን መሪው ለፈፀመው ጥፋትም በፌዴሬሽኑ የዲሲፕሊን መመሪያ መሠረት 6 ጨዋታ እንዲታገድ 5000 ብር ቅጣት እንዲከፍል ወስኗል።


© ሶከር ኢትዮጵያ