ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አዳማ ከተማን ከመመራት ተነስቶ በመጨረሻዎቹ ስድስት ደቂቃዎች ባስቆጠሩት ጎል 2ለ1 በማሸነፍ አንድ ቀሪ ጨዋታ እየቀረው የሊጉ ቻምፒዮን መሆኑን አረጋግጧል፡፡ ክለቡ አሸናፊነቱን እንዲያረጋግጥ ተቀይራ ገብታ ሁለት ግብ ያስቆጠረችው ተስፈኛዋ አጥቂ ፎዚያ መሐመድ ከጨዋታ መጠናቀቅ በኋላ ስሜቷን ለሶከር ኢትዮጵያ አጋርታለች፡፡ ትውልድ እና ዕድገቷ በምዕራብ ጎጃም ዞን ዱርቤቴ በምትባል አካባቢ ነው፡፡ በ2008 ክልሏ አማራን ወክላ በኮፓ ኮካ ኮላ ውድድር ላይ የተሳተፈችው ፎዚያ በውድድሩ ላይ ባሳየችው ተስፋ ሰጪ እንቅስቃሴ በኢትዮጵያ ወጣቶች ስፖርት አካዳሚ ተመልምላለች። በአካዳሚው ሦስት ዓመታትን ሰልጥና ካሳለፈች በኃላ 2011 ላይ በአሰልጣኝ የሺሃረግ ለገሰ ተመልምላ አዲስ አበባ ከተማን በመቀላቀል የክለብ ህይወቷን አንድ ብላ ልትጀምር ችላለች፡፡ በተሰረዘው የ2012 የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪምየር ሊግ ወደ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ መግባት የቻለችው ተስፈኛዋ ዐምና ጉዳት በማስተናገዷ ቡድኗን መጥቀም ባትችልም ዘንድሮ ግን ተቀይራ እየገባች ተስፈኝነቷን እያሳየች ትገኛለች፡፡
© ሶከር ኢትዮጵያ