የአሰልጣኞች አስተያየት | ባህርዳር ከተማ 2-0 ወልቂጤ ከተማ

የአስር ሰዓቱ ጨዋታ በባህር ዳር አሸናኒነት ከተጠናቀቀ በኋላ የሁለቱ ቡድኖች አሰልጣኞች ለሱፐር ስፖርት አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።

ፋሲል ተካልኝ – ባህርዳር ከተማ

ከሁለቱ ግቦች የሚመርጠው

“ከሁለት ቆንጆ ሴቶች አንዱን ምረጥ እንደማለት ነው ፤ ሁለቱም ውብ ናቸው።”

ተመሳሳይ አቀራረብ የሚከተሉ ቡድኖች እንደመሆናቸው በቀላሉ ጨዋታውን አሸንፈናል ብሎ የሚያምን ከሆነ

“አልልም የመጀመሪያው ጎል ለማስቆጠር ረጅም ደቂቃ ጠብቀናል ፤ መሀል ሜዳ ላይ በቁጥር አብዝተው ከጀርባ በሚጣሉ ኳሶች ሊያጠቁን እንደሚችል ገምተናል ግን እኛ ደግሞ ሁል ጊዜ ስንጫወትበት በነበረው መንገድ ቶሎ ቶሎ ለማጥቃት ሞክረን በመጀመሪያ አጋማሽ አልተሳካልንም በሁለተኛው አጋማሽ ክፍተቶችን አግኝተናል ሙሉ ለሙሉ ተጠቅመናል ባልልም ያገኘናቸውን እድሎች ተጠቅመናል።በድሬዳዋ የመጀመሪያ ጨዋታችንን ማሸነፍ ለእኔም ለተጫዋቾቼም ጥሩ ነገር ነው።”

በእረፍት ሰአት ስለነበረው የቡድን ውይይት

“በመጀመሪያ አጋማሽ ስናጠቃበት የነበረውን መንገድ በቀላሉ ሲቆጣጠሩት ነበር ፤ በተለየ መንገድ አንዳንድ ክፍት ቦታዎች ይታዩ ነበር ከውሳኔ ጋር ተያይዞ በአጋማሹ እነሱን መጠቀም አልቻንም ነበር።አንድ ትክክለኛ ኳስ ቢያገኝ ባዬ ጎሉን አስቆጥሯል እና በአጠቃላይ በመጀመሪያው አጋማሽ ከነበረውን የማጥቃት መንገድ በሁለተኛው አጋማሽ ለመቀየር ሞክረናል።”

ወደ ሰንጠረዡ አናት ስለመጠጋታቸው

“ረጅም ነው ጉዞዎ ገና ከፊታችን ስምንት ጨዋታዎች ይቀሩናል ፤ ከፊታችን ፋሲል እያሸነፈ ነው እኔ የምፈልገው በእያንዳንዱ ጨዋታ በአዕምሮም በአካልም ተዘጋጅተን ጨዋታዎችን ማሸነፍ ነው። ማሸነፍ ካለ መጨረሻ ወደምንፈልገበት ቦታ እንደርሳለን ፤ እስከአሁን የመጣንበትን መንገድ እያስቀጠልን ለመሄድ እንጥራለን።”

ደግአረግ ይግዛው -ወልቂጤ ከተማ

በሁለቱ የመሀል ተከላካዮች አለመናበብ ቡድኑን ዋጋ ስለማስከፈሉ

“አዎ ፤ ጨዋታውን እንዳያችሁት መጫወት የፈለግነው ጨዋታ መተግበር ችለናል ብዬ አላስብም።ያው እንግዲህ እግርኳስ ላይ አንዳንዴ እንዲህ አይነት ነገሮች ያጋጥማሉ ፤ በቀጣይ ጨዋታዎች ያሉብን ክፍተቶች አርመን ለመቅረብ የተቻለንን ሁሉ እንሞክራለን።”

ለወትሮው እድሎችን ለመፍጠር የማይቸገረው ቡድን ዛሬ የመጀመሪያውን ኢላማውን የጠበቀ ሙከራ ለማድረግ 60 ደቂቃዎችን መጠበቁ

“እውነት ነው ልጆቹ ይዘነው ስንገባ ሁለት ፈጣን ጉልበት ያላቸው አጥቂዎችን ነው ለመጠቀም የሞከርነው ነገርግን ኳስ ቶሎ ቶሎ እነሱ ጋር አይደርስም ነበር ያ ደግሞ የእነሱ ነፃ ቦታዎችን የመፈለግ እና አማካዮችን የማስገደድ ነገር አልነበራቸውም። በአጠቃላይ ግን ጨዋታውን በምንፈልገው መንገድ ተጫውተነዋል ብዬ አላስብም።”


© ሶከር ኢትዮጵያ