“ዓመቱ ልዩ ነበር…” – አቡበከር ናስር

የዘንድሮ የቤትኪንግ ፕሪምየር ሊግ ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ ተጫዋች የሆነው አቡበከር ናስር የዋንጫ እና የገንዘብ ሽልማቱን ተረክቧል።

29 ግቦችን ያስቆጠረው አቡበከር ናስር የውድድሩ ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ በመሆኑ የዋንጫ እና የ2 መቶ ሺ ብር ሽልማቱን ከክብር እንግዳው ዮርዳኖስ ዓባይ ተቀብሏል። ተጫዋቹም ሽልማቱን ከተረከበ በኋላ ተከታዩን ሀሳብ በመድረኩ ተናግሯል።

“በቅድሚያ ፈጣሪዬን አመሠግናለሁ። ዓመቱ ልዩ ዓመት ነበር። የቡድን አጋሮቼን እና አሠልጣኝ ካሣዬ አራጌንም አመሠግናለሁ። በዋናነትም የቡድን አጋሮቹ እዚህ እንድደርስ ረድተውኛል። በሚቀጥለው ዓመትም የተሻለ ነገር ለማሳለፍ ተስፋ አለን። ቡድናችን ኢትዮጵያ ቡና ቻምፒዮን ለማድረግ አላማ አለን።” ብሏል። ተጫዋቹ ከሚወደው እና ከሚያከብረው ዮርዳኖስ አባይ ሽልማቱን በመቀበሉም ደስታ እንደተሰማው ተናግሮ ሀሳቡን አገባዷል።