“እግርኳሳችን እንዳይሞት ቀድመን መጠንቀቅ አለብን” መቶ አለቃ ፍቃደ ማሞ

የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ የአክሲዮን ማኅበር የቦርድ ሰብሳቢ ከደጋፊዎች ጋር በተያያዘ ሀሳብ ሰጥተዋል።

በአሁኑ ሰዓት በሸራተን አዲስ ሆቴል እየተደረገ በሚገኘው የቤትኪንግ ፕሪምየር ሊግ የመዝጊያ ሥነ-ስርዓት ላይ የሊጉ አክሲዮን ማኅበር የቦርድ ሰብሳቢ መቶ አለቃ ፍቃደ ማሞ ከቀጣይ ዓመት ጀምሮ ደጋፊዎች ወደ ስታዲየም እንዲመጡ መደረግ እንዳለበት ሀሳብ ሰጥተዋል።

“መንግስትን የምንጠይቀው በሚቀጥሉት ዓመታት በምናደርጋቸው ውድድሮች ውስጥ የማኅበራዊ ፈቀቅታን እየጠበቅን ተመልካች በሜዳ ገብቶ ውድድር እንዲመለከት እንዲደረግ ነው። ይህ እንዲሆን ደግሞ በመንግስት በኩል ጥረት መደረግ አለበት። እግርኳስ ያለ ተመልካች ከባህር የወጣ ዓሳ ነው። ይሞታል። እግርኳሳችን እንዳይሞት ደግሞ ቀድመን መጠንቀቅ አለብን። ተመልካቾች በቴሌቪዥን ብቻ ከሚገደቡ የኮቪድ-19 ህግጋት እየጠበቅን ስታዲየም እንዲመጡ ማድረግ እንችላለን። በእግርኳስ የህዝብ አስተባባሪ ነው። እግርኳስ በህዝብ መካከል ፍቅር እንዲከሰት የሚያደርግ ነው። ዛሬ በኢትዮጵያ ላይ የሚያንዣብቡትን ችግሮች ለማረጋጋት እግርኳሱ ጠቃሚ ነው። ስለዚህ ደጋፊዎች ወደ ስታዲየም እንዲመጡ ቢደረግ ጥሩ ነው።”