አቡበከር ናስርን ለማስፈረም የጆርጂያ ክለብ ጥያቄ አቅርቧል

በዘንድሮ የውድድር ዘመን እጅግ ድንቅ ጊዜ ያሳለፈው አቡበከር ናስር ከጆርጂያ ክለብ የእናስፈርም ጥያቄ እንደቀረበለት ተሰምቷል።

በሦስት ዘርፎች የዘንድሮ የቤትኪንግ ፕሪምየር ሊግ ኮከብ ተብሎ ሽልማት የተበረከተለት አቡበከር ናስር የበርካታ የውጪ ክለቦች እይታ ውስጥ መግባቱ እየተሰማ ይገኛል። አሁን በወጣ መረጃ መሠረት ደግሞ የጆርጂያው ክለብ ዲላ ጎሪ ተጫዋቹን የግሉ ለማድረግ የተጫዋቹ ባለቤት ኢትዮጵያ ቡናን በይፋዊ ደብዳቤ ጠይቋል።

ዲላ ጎሪ የተባለው ክለብ ከሦስት ቀናት በፊት በላከው ደብዳቤ ላይም ተጫዋቹን ለማስፈረም በሚቻልበት መንገድ ሁሉ ጥረት ለማድረግ ፍላጎት እንዳለው አውስቶ ለድርድርም ፍቃደኛ እንደሆነ ገልጿል። በደብዳቤው ላይ እንደሰፈረው ፅሁፍ ከሆነም አቡበከር የህክምና ፈተናውን ካለፈ በቋሚ ኮንትራት ተጫዋቹን ለማስፈረም ፍላጎት እንዳላቸው አብራርተዋል። በክለቡ ዋና ሥራ አስኪያጅ ስም በወጣው የክለቡ ደብዳቤ ኢትዮጵያ ቡና በቶሎ ምላሽ እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል።