ድሬዳዋ ከተማ የአሰልጣኙን ኮንትራት አራዘመ

ድሬዳዋ ከተማን በውድድር ዘመኑ አጋማሽ ተረክበው ሲያሰለጥኑ የነበሩት አሰልጣኝ ዘማርያም ወልደጊዮርጊስ ውላቸውን አድሰዋል።

በ2013 የኢትዮጵያ ቤትኪንግ ፕሪምየር ሊግ አስቸጋሪ የውድድር ዓመትን ካሳለፉ ክለቦች መካከል አንዱ የነበረው ድሬዳዋ ዓመቱን በአሰልጣኝ ፍሰሐ ጥዑመልሳን እየተመራ መጀመር ቢችልም በውድድር ዘመኑ አጋማሽ ላይ በውጤት መጥፋት ምክንያት ከአሰልጣኙ ጋር ከተለያየ በኃላ የቀድሞው የአዳማ፣ ፋሲል ከነማ፣ ወልድያ፣ ጅማ አባጅፋር እና ወልዋሎ አሰልጣኝ የነበሩት ዘማርያም ወልደጊዮርጊስን በቦታው መተካት የቻለ ሲሆን አሰልጣኙም ቡድኑን በሊጉ የማቆየት ኃላፊነታቸውን በመወጣት ለቀጣዩ ዓመት በሊጉ መቆየት እንዲችሉ ማድረግ በመቻላቸው በአሰልጣኙ እና ቦርዱ መካከል ሲደረግ የነበረው ድርድር ተጠናቆ ለቀጣዮቹ ሁለት ዓመታት በክለቡ ለመቆየት ፊርማቸውን ማኖራቸውን ክለቡ አስታውቋል፡፡

አሰልጣኙ ውል ማደሳቸውን ተከትሎ በአዳዲስ ተጫዋቾች ቡድኑን ለማዋቀር እንቅስቃሴ እንደሚጀምሩ ለማወቅ ተችሏል።