ሲዳማ ቡና ተጨማሪ ተጫዋች አስፈርሟል

ዘንድሮ ከቀደመው ጊዜያት ተዳክሞ የቀረበው ቡድናቸውን ለማጠናከር በዝውውር መስኮቱ ጠንካራ ሥራዎችን እየሰሩ የሚገኙት ሲዳማ ቡናዎች የተከላካይ መስመር ተጫዋቾች አስፈርመዋል።

የቀድሞው የኢትዮጵያ ቡና፣ መከላከያ፣ አዳማ ከተማ፣ መቐለ 70 እንደርታ እና በተጠናቀቀው የውድድር ዘመን በሀዲያ ሆሳዕና ያሳለፈው ተስፋዬ በቀለ የቡድኑ አራተኛ ፈራሚ ሆኖ ቡድኑን ተቀላቅሏል። የተጫዋቹ መፈረምም በቀላሉ ግብ ያስተናግድ ለነበረው የሲዳማ ቡና የተከላካይ መስመር ልምድ እና ጥንካሬን ያላብሳል ተብሎ ይጠበቃል።

ቡድኑ ዛሬ ረፋድ ሁለት ተጫዋቾችን ከከፍተኛ ሊጉ ኮልፌ ቀራንዮ ያስፈረመ ሲሆን አስቀድሞም የኢትዮጵያ ቡናውን የግብ ዘብ ተክለማርያም ሻንቆን ወደ ቡድኑ መቀላቀሉ ይታወሳል።

ቡድኑ በቀጣዩቹ ቀናት የአንድ የመስመር ተከላካይ እና የተከላካይ አማካይ ለማዛወር እንደተሰማማ ሲታወቅ እንዲሁ ከአሰልጣኝ ገብረመድኅን ኃይሌ ጋርም በመጪዎቹ ሁለት ቀናት በይፋ በክለቡ የሚያቆየውን ስምምነት ያሥራል ተብሎ ይጠበቃል።