ሰበታ ከተማ የመጀመሪያ ተጫዋቹን አስፈረመ

አሰልጣኝ ዘላለም ሽፈራውን በትናንትናው ዕለት በይፋ የቀጠረው ሰበታ ከተማ የአጥቂው መስመር ተጫዋቹን የመጀመሪያው ፈራሚ አድርጓል፡፡

አሰልጣኝ አብርሀም መብራቱን ለባህር ዳር ከተማ አሳልፎ ከሰጠ በኃላ የአሰልጣኝ ቅጥር ማስታወቂያ በማውጣት ሲያወዳድር የነበረው ሰበታ ከተማ በትናንትናው ዕለት ከተወዳደሩት አስር አሰልጣኞች መካከል ዘላለም ሽፈራውን በቦታው ምርጫው ማድረጉን ዘግበን ነበር፡፡ ክለቡም የአሰልጣኙን ቅጥር ከፈፀመ በኃላ በዛሬው ዕለት ወደ ዝውውር ገብቶ አጥቂው ዘካሪያስ ፍቅሬ ክለቡን የተቀላቀለው ቀዳሚው ፈራሚ ሆኗል፡፡

የቀድሞው የአርባምንጭ ከተማ፣ ሀላባ ከተማ፣ ድሬዳዋ ከተማ ከተማ እና እክሱም ከተማ ተጫዋች በተጠናቀቀው የውድድር ዓመት አክሱምን ከለቀቀ በኃላ ወደ መከላከያ አምርቶ ዓመቱን በክለቡ አሳልፏል፡፡ በከፍተኛ ሊግ በተከታታይ ኮከብ አግቢ በመሆን የሚታወቀው እና መከላከያ ወደ ፕሪምየር ሊጉ በቀጣዩ ዓመት ተሳታፊ መሆኑን ሲያረጋግጥ ከፍተኛ ድርሻን ጎሎችን በማስቆጠር ያደረገው አጥቂው በቀጣዩ ዓመት ወደ ሰበታ አምርቶ ለመጫወት ፊርማውን ለሁለት ዓመት አስፍሯል፡፡