ጅማ አባጅፋር ተጨማሪ ሁለት ተጫዋቾችን አስፈርሟል

ከሰዓታት በፊት እያሱ ለገሠን የግሉ ያደረገው ጅማ አባጅፋር አሁን ደግሞ የሁለት ተጫዋቾችን ዝውውር አጠናቋል።

ቡድኑን የተቀላቀለው የመጀመሪያው ተጫዋች ተስፋዬ መላኩ ነው። የቀድሞው የወላይታ ድቻ፣ ኤሌክትሪክ እና ሀዋሳ ከተማ ሁለገብ ተጫዋች የሆነው ተስፋዬ ለአንድ ዓመት ከስድስት ወራት በወልቂጤ ከተማ ቆይታ ያረገ ሲሆን አሁን ደግሞ በ2011 ተጫውቶ ወዳሳለፈበት ጅማ አባ ጅፋር አምርቷል።

ሁለተኛው ተጫዋች ደግሞ የግብ ዘቡ ዩሐንስ በዛብህ ነው። የንግድ ባንክ፣ ሀዋሳ ከተማ፣ ኢትዮጵያ ቡና እና ኤሌክትሪክ ግብ ጠባቂ የተጠናቀቀውን የውድድር ዓመት በወልቂጤ ከተማ ማሳለፉ ይታወቃል። አሁን ደግሞ እንደ ቡድን አጋሩ ተስፋዬ ሁሉ መዳረሻው ጅማ ሆኗል።

በኤሌክትሪክ እና ወልቂጤ የቡድን አጋር የነበሩት ሁለቱ ተጫዋቾች ለሦስተኛ ጊዜ በአንድ ቡድን የሚገናኙ ይሆናል።