አዲሱ የቅዱስ ጊዮርጊስ አሰልጣኝ ቅዳሜ አዲስ አበባ ይገባሉ

ከሳምንታት በፊት የቅዱስ ጊዮርጊስ አሰልጣኝ ሆነው የተሾሙት ሰርቢያዊ ቅዳሜ አዲስ አበባ እንደሚገቡ ይፋ ተደርጓል።

የ64 ዓመቱ ሰርቢያዊ ዝላትኮ ክራምፖቲች በዋና አሰልጣኝነት የሾሙት ቅዱስ ጊዮርጊሶች አዲሱ አሰልጣኝ ከሰርቢያዊው ምክትላቸው ኒኮላ ኮሮሊጃ ጋር በመሆን በመጪው ቅዳሜ አዲስ አበባ እንደሚገቡ ያስታወቀ ሲሆን በተመሳሳይ ዕለት የዋናው ቡድን አባላት በዘሪሁን ሸንገታ እየተመሩ ለቅድመ ውድድር ዝግጅት ቢሾፍቱ ወደሚገኘው የክብር ይድነቃቸው ተሰማ አካዳሚ እንደሚከትሙም ክለቡ በይፋዊ የሬዲዮ ፕሮግራም ይፋ አድርጓል።

በቀጣዩ ቀናት አዳዲሶቹ አሰልጣኞች ከክለቡ አመራሮች እና የቡድን አባላት ጋር ትውውቅ እንደሚያደርጉ ሲጠበቅ በመጪው ሰኞም አሰልጣኙ በክለቡ ፅህፈት ቤት በሚደረግ ይፋዊ ጋዜጣዊ መግለጫ አሰልጣኙን በይፋ እንደሚያስተዋውቁ ተገልጿል።