አሰልጣኝ ካሣዬ ወደ አዲስ አበባ አምርተዋል

ከሳምንት በፊት ወደ ቢሸፍቱ አቅንተው የነበሩት አሰልጣኝ ካሣዬ አራጌ ወደ አዲስ አበባ መመለሳቸው ተሰምቷል።

የምክትል አሰልጣኙ ውል አለመራዘም ተከትሎ ደስተኛ ያልሆኑት የኢትዮጵያ ቡናው አሰልጣኝ ካሣዬ አራጌ ቡድኑ ለዝግጅት ወደ ቢሸፍቱ ባመራበት ወቅት አብረው ሳይጓዙ በመቅረታቸው በክለቡ እና በአሰልጣኙ መካከል አለመግባባት ተፈጥሮ ቢቆይም በኋላ ላይ ክለቡ ሥራቸውን እያከናወኑ ጥያቄያቸው እንደሚታይ ባስቀመጠው አቅጣጫ መሠረት ከስምምነት ደርሰው የትናንት ሳምንት ቡድኑን በመቀላቀል ሲያዘጋጁ ቆይተዋል።

የክለቡ ሥራ አመራር ቦርድ ባሳለፍነው ዓርብ ባደረገው መደበኛ ስብሰባ በምክትል አሰልጣኙ ዙርያ እልባት ለመሰጠት በማሰብ ከተወሰኑ የክለቡ የቦርድ አባላት ጋር ዛሬ ለመነጋገር አሰልጣኝ ካሣዬ ወደ አዲስ አበባ መመለሳቸውን ሰምተናል።

የውይይቱ በምን ይቋጯል የሚለው ነጥብ ተጠባቂ ሲሆን ሶከር ኢትዮጵያ ከሁለቱ አካላት ውይይት በኋላ መረጃው እንደደረሳት ይዛ እንደምትመለሰ ከወዲሁ እንገልፃለን።