የአማካይ መስመር ተጫዋቹ ከዋልያው ስብስብ ውጪ ሆኗል

ከሦስት ቀናት በፊት በልምምድ ላይ ጉዳት ያጋጠመው የአማካይ መስመር ተጫዋች ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ስብስብ ውጪ ሆኗል።

በአሠልጣኝ ውበቱ አባተ የሚመራው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ለኳታሩ የዓለም ዋንጫ ለማለፍ ከጋና እና ዚምባቡዌ ጋር ከያዝነው ወር መጨረሻ ጀምሮ ጨዋታ ያደርጋል። ከሳምንት በፊት ለ28 ተጫዋቾች ጥሪ በማድረግ ልምምድ የጀመረው ቡድኑም ማክሰኞ ወደ አዳማ በማቅናት ልምምድ እንደጀመረ ይታወቃል።

ሶከር ኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድኑ የረቡዕ አመሻሽ ልምምዱን ሲሰራ በስፍራው ተገኝታ እንደዘገበችውም የመሐል ሜዳ ተጫዋቹ ሀብታሙ ተከስተ ከሌላ ተጫዋች ጋር ጉዳት አስተናግዶ ከሜዳ ወጥቶ ነበር። ድረ-ገፃችን የተጫዋቹን የጉዳት ምንነት እና መጠን ለማጣራት ያደረገችው ጥረት ለአሁን ባይሳካም ተጫዋቹ ባጋጠመው ጉዳት ከስብስቡ ሙሉ ለሙሉ ውጪ እንደሆነ ተረድታለች።