የጋና እና ኢትዮጵያ ጨዋታ በሞሮካዊ ዳኞች ይመራል

በዓለም ዋንጫ ማጣሪያ ጋና ኢትዮጵያን የምታስተናግድበት ጨዋታ በሞሮኮ ዳኞች ይመራል፡፡

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ለ2022 የካታር ዓለም ዋንጫ ማጣሪያ ከዚምባብዌ ፣ ጋና እና ደቡብ አፍሪካ ጋር መደልደሏ ይታወሳል፡፡ በያዝነው ወር መጨረሻ የማጣሪያ ጨዋታዎቹ የሚጀመሩ ሲሆን ሀገራችን ኢትዮጵያም ከጋና ጋር ለምታደርገው መርሀግብር በአሰልጣኝ ውበቱ አባተ መሪነት በአዳማ ከተማ ዝግጅት በማድረግ ላይ ትገኛለች፡፡የመጀመሪያውን ጨዋታ ከሜዳዋ ውጪ ጳጉሜ 3 በጋና በኬፕ ኮስት ስታዲየም ዕለተ ዕርብ ምሽት 1፡00 ላይ የምታደርግ ሲሆን ይህን ጨዋታ የሞሮኮ ዜግነት ያላቸው ዳኞች እንዲመሩት ካፍ መርጧል፡፡

በዋና ዳኝነት የ42 አመቱ ጄይድ ሬድዋንስ ሲመሩት በረዳት ዳኝነት አዝጋው ላህሰን እና አከርካርድ ሙስጠፋ፣ በአራተኛ ዳኝነት ደግሞ ጃይድ ጃላላ ይመሩታል፡፡ የጨዋታው አሰሰር በመሆን ቶጓዊው ላውሰን ሆግባን፣ በኮሚሽነርነት ደግሞ ጎሜዝ ማርቲን ከጋምቢያ መሆናቸው ታውቋል፡፡