የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ድልድል ወጥቷል

በካሜሩን አስተናጋጅነት በሚካሄደው 33ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ውድድር የሚሳተፉ ሀገራት የምድብ ድልድላቸውን አውቀዋል።

ከምሽቱ ሦስት ሰዓት ጀምሮ በካሜሩን በተከናወነው የእጣ ማውጣት ሥነ-ስርዓት ላይ የካፍ ፕሬዝዳንት ፓትሪክ ሙሴፔን (ዶ/ር) ጨምሮ የፌዴሬሽን አመራሮች፣ የቀድሞ ተጫዋቾች እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል። የካፍ የውድድር ዳይሬክተር ሳምሶን አዳሙ የቀድሞ ተጫዋቾቹን ሳሙኤል ኢቶ፣ ጋዬል ኢንጋናሙቲ፣ ራባህ ማጄር፣ ዲዲየር ድሮግባ እና አሳሙዋ ጂያንን እየመራ በወጣው ድልድልም ሀያ አራቱ ተሳታፊ ሀገራት በስድስት ምድቦች እንዲቀመጡ ተደርጓል። በዚህም መሠረት:-

ምድብ አንድ

ካሜሩን፣ ቡርኪና ፋሶ፣ ኢትዮጵያ፣ ኬፕ ቬርድ

ምድብ ሁለት

ሴኔጋል፣ ዚምባብዌ፣ ጊኒ፣ ማላዊ

ምድብ ሦስት

ሞሮኮ፣ ጋና፣ ኮሞሮስ፣ ጋቦን

ምድብ አራት

ናይጄርያ፣ ግብፅ፣ ሱዳን፣ ጊኒ ቢሳው

ምድብ አምስት

አልጄርያ፣ ሴራ ሊዮን፣ ኢኳቶሪያል ጊኒ፣ ኮትዲቯር

ምድብ ስድስት

ቱኒዚያ፣ ማሊ፣ ሞሪታኒያ፣ ጋምቢያ

ከስምንት ዓመታት በኋላ ወደ አፍሪካ ዋንጫው የተመለሰው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ጥር 1 2014 ላይ በኦሌምቤ ስታዲየም ከኬፕ ቨርዴ ጋር የመጀመሪያ ጨዋታውን ያከናውናል። ከአራት ቀናት በኋላ (ጥር 5) ደግሞ እዛው ያውንዴ ከተማ በሚገኘው ኦሌምቤ ስታዲየም ከውድድሩ አስተናጋጅ ካሜሩን ጋር የሚጫወት ይሆናል። ብሔራዊ ቡድኑ የመጨረሻ የምድብ ጨዋታውንም ጥር 9 ወደ ባፉሳም አቅንቶ በኮውኮንግ ስታዲየም ከቡርኪና ፋሶ ጋር የሚያደርግ ይሆናል።