የአማካይ ስፍራ ተጫዋቹ ለህፃናት ማሳደጊያ ድጋፉ አድርጓል

አዲሱ የሀዲያ ሆሳዕና የመሐል ሜዳ ተጫዋች ወላጅ አልባ የሆኑ ህፃናትን ለሚያሳድግ ተቋም ድጋፉ ማድረጉ ታውቋል፡፡

የሀገራችን እግር ኳስ ተጫዋቾች ይነስም ይብዛ እንደ አቅማቸው እና ፍቃዳቸው በሚኖሩባቸው አካባቢዎች የተለያዩ መልካም ተግባራትን ሲፈፅሙ እናስተውላለን፡፡ ከትናንት በስቲያ አዲሱ የሲዳማ ቡና ተጫዋች ፍሬው ሠለሞን አቤኔዘር ለተባለ እና ወላጅ አጥ የሆኑ ህፃናትን የሚያሳድግ ማዕከል በመገኘት ምግብ ነክ የሆኑ ድጋፎችን ያደረገ ሲሆን አሁን ደግሞ ሌላኛው የአማካይ ስፍራ ተጫዋች ለዚሁ ተቋም ተመሳሳይ መልካም ተግባርን ፈፅሟል፡፡

የቀድሞው የደቡብ ፓሊስ እንዲሁም ሲዳማ ቡናን በያዝነው ወር በመልቀቅ ወደ ሀድያ ሆሳዕና ያቀናው አማካዩ አበባየው ዮሐንስ ሀዋሳ በሚገኘው የህፃናት ማሳደጊያው በመገኘት ምግብ ነክ የሆኑ ቁሶችን በማበርከት ድጋፉ ማድረጉ ታውቋል፡፡