ሰበታ ከተማ አንበሎቹን አሳውቋል

ሰበታ ከተማ ለ2014 ከቡድኑ ጋር አብረው ያልዘለቁትን የሚተኩ አዲስ አንበሎችን ሾሟል።

በአሰልጣኝ ዘላለም ሽፈራው ለቀጣይ ሦስት ዓመት የሚመራው ሰበታ ከተማ ከዚህ ቀደም በቡድኑ ውስጥ የአንበልነት ሚናቸውን ከሚወጡ ተጫዋቾቹ ጋር ከኮንትራታቸው መጠናቀቅ ጋር ተያይዞ መለያየቱ ይታወቃል። ይህን ተከትሎ ለቀጣይ የውድድር ዘመን በአንበልነት የሚመሩ ተጫዋቾችን መምረጥ ግዴታ ውስጥ የገቡት አሰልጣኝ ዘላለም ሽፈራው ጌቱ ኃይለማርያም እና ለዕለም ብርሀንን አንደኛ እና ሁለተኛ አንበል አድርገው መሾማቸውን አሳውቀውናል።

ቡድኑን ከታችኛው እርከን አንስቶ ከፍተኛ አገልግሎት በመስጠት አንበልም በመሆን እየመራ የቆየው ጌቱ ኃይለ ማርያም አሁንም የአሰልጣኝ ዘላለም የመጀመርያ አንበል በመሆን እንደሚቀጥል ታውቋል።

ሌላኛው ሁለተኛ ተመራጭ በመሆን የተሰየመው ለዓለም በሲዳማ ቡና ለአራት ዓመት ሲጫወት በአንበልነትም ጭምር ያገለገለ ሲሆን ከቅዱስ ጊዮርጊስ ከለቀቀ በኋላ ወደ ሰበታ ከተማ በዚህ ክረምት ማምራቱ ይታወሳል።

በሌላ ዜና ቋሚ የግብጠባቂ አሰልጣኝ ያልቀጠረው ሰበታ ከተማ በቅርቡ ወደ ክለቡ አዲስ የግብጠባቂ አሰልጣኝ እንደሚሾም ሰምተናል።