የዋልያዎቹ ተጋጣሚ ስብስቧን አሳውቃለች

በዓለም ዋንጫ የምድብ ማጣርያ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድንን የሚገጥመው የዚምባብዌ ብሔራዊ ቡድን ስብስቡን አሳውቋል።

የ2022 የዓለም ዋንጫ የአፍሪካ ዞን ጨዋታዎች ከወሩ መጨረሻ ጀምሮ መከናከናቸውን ይጀምራሉ። ከጋና፣ ደቡብ አፍሪካ እና ዚምባብዌ ጋር የተደለደለችው ኢትዮጵያም ወደ ኬፕ ኮስት አምርታ ጋናን በመግጠም የምትጀምር ሲሆን ከሦስት ቀናት በኋላ ዚምባብዌን በባህር ዳር ስታዲየም ታከናውናለች።

ጳጉሜ 2 ከኢትዮጵያ ጋር ሁለተኛ የምድብ ጨዋታዋን የምታደርገው ዚምባብዌ ከዋልያዎቹ በፊት ደቡብ አፍሪካን የምትገጥም ሲሆን ለጨዋታዎቹ እንዲረዳትም ከሌሎቹ ሀገራት በዘገየ መልኩ ስብስቧን ዛሬ አሳውቃለች። ቡድኑ በመጀመርያ ሀያ ዘጠኝ ተጫዋቾችን ይፋ አድርጎ የነበረ ቢሆንም አጥቂው ዶቤ ፕሪንስ በጉዳት ከስብስቡ ውጪ ሆኖ ብለሲንግ ሳሩፒንዳ ተተተክቷል።

በዌሊንግተን ምፓንዳሪ የሚመሩት “ማይቲ ዋርየርስ” ስብስብ ውስጥ የአልታኢው አጥቂ ኖውሌጅ ሞሱና፣ የሊዮኑ ቲዮቴንዳ ካድዌሬ፣ የአስቶን ቪላው ማርቭለስ ናካምባ፣ የካይዘር ቺፍሱ ካማ ቢሊያት የሚጠቀሱ ስሞች ናቸው።