ቶጎዋዊው አጥቂ ፈረሰኞቹን በይፋ ተቀላቅሏል

ቅዱስ ጊዮርጊስን ለመቀላቀል ከጫፍ እንደደረሰ በሶከር ኢትዮጵያ ዘግበን የነበረው ቶጎዋዊው አጥቂ ክለቡን በይፋ ተቀላቅሏል።

በስርቢያዊው አሠልጣኝ ዝላትኮ ክራምፖቲች እየተመሩ የቅድመ ውድድር ዝግጅታቸውን ከሳምንት በፊት የጀመሩት ቅዱስ ጊዮርጊሶች አጥቂ እና ግብ ጠባቂ ከቶጎ እና ዩጋንዳ ለማስፈረም መስማማታቸውን ድህረ-ገፃችን ከዚህ ቀደም ዘግባ ነበር። ይህንን ተከትሎም አሁን ክለቡ ይፋ ባደረገው መረጃ ከሰሞኑን ወደ አዲስ አበባ ለመምጣት የተስማማው ቶጎዋዊው አጥቂ እስማኤል ኦሮ-አጎሮ የሁለት ዓመት ውል ፊርማ አኑሯል።

የ25 ዓመቱ የመሐል አጥቂ ኦምኒስፖርትስ አጋዛ እና ኤ ኤስ ሲ ካራ ለተባሉ የሀገሩ ክለቦች ተጫውቶ ማሳለፉ ሲታወስ ቶጎንም ባሳለፍነው የቻን ውድድር አገልግሏል። ትናንት ምሽት አዲስ አበባ የገባው ተጫዋቹም ዛሬ ወደ ቢሾፍቱ በማቅናት ስብስቡን የተቀላቀለ ሲሆን በነገው ዕለትም መደበኛ ልምምዱን ከአዲሶቹ አጋሮቹ እንደሚጀምር ተጠቁሟል።