የቀድሞ የፈረሰኞቹ የግብ ዘብ የሀገሩን ክለብ ተቀላቅሏል

ለሦስት ዓመታት በቅዱስ ጊዮርጊስ መለያ ግልጋሎት የሰጠው ግብ ጠባቂ የሀገሩን ክለብ ዳግም ተቀላቅሏል።

ኬንያዊው ግብ ጠባቂ ፓትሪክ ማታሲ 2011 ላይ ወደ ኢትዮጵያ ከመጣ በኋላ የመዲናውን ክለብ በጥሩ ብቃት ሲያገለግል እንደነበር ይታወሳል። እርግጥ በተጠናቀቀው የውድድር ዓመት ጅማሮ ላይ ባሳየው ደካማ ብቃት ከስብስቡ ውጪ እንዲሆን የተደረገው ግብ ጠባቂውም በሊጉ የመጨረሻ ጨዋታዎች ላይ በባህሩ ነጋሽ መንበሩን ተነጥቆ በተጠባባቂ ወንበር ላይ ሲያሳልፍ እንደነበር ይታወሳል።

የቀድሞ የሊዮፓርድስ እና ፖስታ ሬንጀርስ ግብ ጠባቂ የነበረው ማታሲ ወደ ፈረሰኞቹ ከመምጣቱ በፊት ለተስከር ፊርማውን አኑሮ እንደነበር ይታወቃል። አሁን ደግሞ ከቅዱስ ጊዮርጊስ ጋር ያለው ውል መጠናቀቁን ተከትሎ በሁለት ዓመት ውል የቀድሞ ክለቡ ተስከርን መቀላቀሉ ይፋ ሆኗል።