ጌታነህ ከአንድ የፕሪምየር ሊግ ቡድን ጋር ልምምድ ጀመረ

በትናትናው ዘገባችን ከሲዳማ ቡና ጋር ድርድር መጀመሩን ዘግበን የነበርነው ጌታነህ ከቀድሞ አሰልጣኙ ክለብ ጋር ልምምድ መጀመሩ ታውቋል።

ቀሪ የአንድ ዓመት ኮንትራት እያለው ፈረሰኞቹ ጋር የመለያየቱ ነገር እርግጥ የሆነው የዋልያዎቹ አንበል ጌታነህ ከበደ ቀጣይ ማረፊያው የት ይሆናል በሚል በትናትናው ምሽት ዘገባችን ለጊዜው ከስምምነት አይድረሱ እንጂ ከሲዳማ ቡና አመራሮች ጋር መነጋገሩን ገልፀን ነበር። ከሲዳማ ጋር ያለው ድርድር ያልተቋጨ ቢሆንም ዛሬ ጠዋት ጌታነህ ከበደ ዝግጅቱን በሀዋሳ ከተማ እያከናወነ ከሚገኘው ሰበታ ከተማ ጋር ልምምድ ሲሰራ መቆየቱን አረጋግጠናል።

በትናትናው ምሽት ከአሳዳጊው የቀድሞ አሰልጣኙ ዘላለም ሽፈራው ጋር ወደ ሰበታ ከተማ በሚያቀናበት ጉዳይ ዙርያ ንግግሮች ማድረጉን የሰማን ሲሆን ውይይቱ ፍሬ አፍርቶ ሰበታን ለመቀላቀል ተስማምቶ ይሁን ? ለጊዜው አብሮ ልምምድ ለመስራት ፈልጎ ይሁን ? ለአሁን ያገኘነው የተረጋገጠ መረጃ የለም። ሆኖም ግን ሰበታ ከተማ ጌታነህን ለማስፈረም ከፍተኛ ፍላጎት እያሳየ መምጣቱን ሰምተናል።