ሀዋሳ ከተማ አምስት ተጫዋቾችን ሲያሳድግ የወጣቱን አጥቂ ውልም አድሷል

የቅድመ ውድድር ዝግጅታቸውን እየሰሩ የሚገኙት ሀዋሳ ከተማዎች አምስት ወጣቶችን ወደ ዋናው ቡድን ሲያሳድጉ የወጣት ተጫዋቻቸውን ውልም አራዝመዋል፡፡

በኢትዮጵያ እግር ኳስ ውስጥ ታዳጊ ወጣቶችን በማብቃቱ ረገድ ሊጠቀሱ ከሚችሉ ውስን ክለቦች መካከል አንዱ የሆነው ሀዋሳ አምስት ወጣቶችን በአሰልጣኝ እስራኤል ጊነሞ ከሚመራው ከ20 ዓመት በታች የሀዋሳ ቡድን ያሳደገ ሲሆን ብሩክ ዓለማየሁ (አማካይ)፣ አስችሎም ኤልያስ (አማካይ)፣ ሚኪያስ ታምራት (ተከላካይ)፣ ታምራት ተስፋዬ (ተከላካይ) እና ፍቃደሥላሴ ደሳለኝ (ተከላካይ) መሆናቸውን ሶከር ኢትዮጵያ አረጋግጣለች።

በ2010 በዩጋንዳ ተዘጋጅቶ በነበረው የሴካፋ ከ17 ዓመት በታች ዋንጫ ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ተሰልፎ በመጫወት የውድድሩ ከፍተኛ ግብ አግቢ የነበረው እና በሀዋሳ ከ17 እና ከ20 ዓመት በታች ቡድን ውስጥ ከተጫወተ በኋላ በ2012 ወደ ዋናው የሀዋሳ ቡድን ያደገው የአጥቂ ስፍራ ተጫዋቹ ምንተስኖት እንድሪያስ ለተጨማሪ ዓመት ውሉ በክለቡ ታድሶለታል፡፡