ሴቶች ፕሪምየር ሊግ | አዲስ አበባ ከተማ አዳዲስ ተጫዋቾችን ሲያስፈርም የነባሮችንም ውል አድሷል

አዲስ አበባ ከተማ ዘጠኝ አዳዲስ ተጫዋቾችን ሲያስፈርም የአስራ ሦስቱን ውል አድሷል፡፡

በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪምየር ሊግ አንደኛ ዲቪዚዮን ስር በመወዳደር ላይ የሚገኘው አዲስአበባ ከተማ ለቀጣዩ የ2014 የውድድር ዓመት ጊዜያዊ አሰልጣኝ የነበረችው የሺሀረግ ለገሰን በዋና አሰልጣኝነት እንድትቀጥል ሲያደርግ ዘጠኝ ተጫዋቾችን ከተለያዩ ክለቦች ማስፈረም እና በክለቡ የነበሩ አስራ ሦስት ተጫዋቾች ደግሞ ውላቸውን ማደስ ችሏል፡፡

የቀድሞዋ የመከላከያ እና እንዲሁም በአዳማ ከተማ ያለፉትን ዓመታት ያሳለፈችው አጥቂዋ ብሩክታዊት አየለ፣ የተጠናቀቀውን የውድድር ዓመት በኢትዮ ኤሌክትሪክ ቆይታ የነበራት የመሀል ተከላካይዋ ፋሲካ በቀለ፣ የአጥቂ አማካይዋ ዘይነባ ሰይድ (ባህርዳር ከተማ)፣ አማካይዋ ንግስት ኃይሉ (አቃቂ ቃሊቲ) ፣ ተከላካዮቹ  ማክዳ ዓሊ (አቃቂ ቃሊቲ) እና ቤተልሄም ከፍያለው ( መቐለ 70 እንደርታ)፣ የቀደሞ የቡድኑ ግብ ጠባቂ የነበረችው ስርጉት ተስፋዬ (አቃቂ ቃሊቲ)  እንዲሁም በአርባምንጭ ከተማ ተስፋ ሰጪ እንቅስቃሴ ስታሳይ የነበረችው ግብ ጠባቂዋ ድንቡሽ አባ እና የቦሌ ክፍለከተማ ተከላካይ ሀና አዲስ አበባን መቀላቀል የቻሉ ተጫዋቾች ሆነዋል፡፡

ውል ያራዘሙ ተጫዋቾች 

ለአዳማ ከተማ ለመጫወት ቀደም ብለው ስምምነት ፈፅመው የነበሩት ተከላካዮቹ በሻዱ ረጋሳ እና የውብዳር መስፍን በድጋሚ ተመልሰው በአዲስ አበባ ለመቀጠል ለአንድ ተጨማሪ ዓመት ውል ያራዘሙ ሲሆን ዮርዳኖስ ፍሰሐ (ተከላካይ)፣ ሩታ ያደታ (ተከላካይ)፣ ቤተልሄም ዮሐንስ (ግብ ጠባቂ) ፣ መሰረት ገ/እግዚአብሔር (አማካይ) ፣ ፍቅርተ አሰማማው ( አማካይ)፣ የምወድሽ አሸብር (አማካይ) ፣ ሰላማዊት ኃይሌ (አማካይ)፣ መሰታወት አመሎ (አማካይ)፣ ፍሬወይኒ ገብረእግዚአብሔር (አማካይ)፣ ትርሲት መገርሳ (አማካይ) እና ቤቴልሄም ሰማን (አጥቂ) ውል ያራዘሙ ተጫዋቾች  ናቸው፡፡