የፈረሰኞቹ አጥቂ በቅርቡ ወደ ሜዳ ይመለሳል

ለወራት በጉዳት ላይ የቆየው የቅዱስ ጊዮርጊሱ አጥቂ በቅርቡ ወደ ሜዳ እንደሚመለስ ሰምተናል።

ሲዳማ ቡናን ለቆ አምና ወደ ቅዱስ ጊዮርጊስ በማምራት በሁለት ዓመት ኮንትራት ለመጫወት ፊርማውን ያኖረው አዲስ ግደይ ከጉዳት ጋር በተያያዘ የታሰበውን ግልጋሎት ሳይሰጥ መቆየቱ ይታወቃል። የዋልያዎቹ የመስመር አጥቂ መጋቢት ወር ላይ ቡድኑ ቅዱስ ጊዮርጊስ ከቀድሞ ክለቡ ሲዳማ ቡና ጋር ባደረገው የአቋም መለኪያ ጨዋታ ወቅት የጉልበት ጉዳት አስተናግዷል።

ከስድስት ወር በላይ በጉልበት ጉዳት ምክንያት ከሜዳ የራቀው አዲስ ግደይ አሁን ህክምናውን በአግባቡ በመከታተል የጤና መሻሻል ማሳየቱን እና የጂም እና ቀለል ያሉ ልምምዶችን መጀመሩን ገልፆልናል።

አዲስ ቀለል ያሉ ልምምዶች መጀመሩን ተከትሎ ምንም አንኳ በትክክል መቼ ወደ ሜዳ የሚመለስበት ቀን ባይታወቅም ምናልባትም ሊጉ ከኢንተርናሽናል ውድድር ሲመለስ ግልጋሎት መስጠት ሊጀምር እንደሚችል ሲጠበቅ ተጫዋቹም ወደ አቋሙ በመመለስ ክለቡንም ሆነ ሀገሩን የማገልገል ከፍተኛ ፍላጎት እንዳለው ነግሮናል።