ቤትኪንግ የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ – የሁለተኛ ሳምንት ቁጥሮች እና ዕውነታዎች

በ2014 ቤትኪንግ የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ሁለተኛ ሳምንት በተደረጉ ጨዋታዎች ላይ የተመዘገቡ ቁጥራዊ መረጃዎች እና እውነታቸዎች እንዲህ ቀርበዋል።

የጎል መረጃዎች

– በዚህ ሳምንት በተደረጉ ስምንት ጨዋታዎች 16 ጎሎች ተቆጥረዋል። በአማካይ 2 ጎል በጨዋታ ያስተናገደው ይህ ሳምንት ካለፈው ሳምንት በአራት የላቀ ጎል ተመዝግቦበታል።

– ከተቆጠሩት መካከል አንድ ከቀጥታ ቅጣት ምት (ዳዋ ሆቴሳ) ሲያስቆጥር ሁለት (ወርቅይታደስ አበበ እና ሐይደር ሸረፋ) በፍ/ቅ/ም አስቆጥረዋል። ቀሪዎቹ ግቦች ከክፍት እንቅስቃሴ መነሻነት ተቆጥረዋል።

– በዚህ ሳምንት ሦስት የፍፁም ቅጣት ምቶች ተተመትተው ጌታነህ ከበደ በሚኬል ሳማኬ ሲመለስበት ወርቅይታስ እና ሐይደር አስቆጠረዋል።

– ሐይደር ሸረፋ እና ይገዙ ቦጋለ 2 ግቦች ያስቆጠሩ ተጫዋቾች ሲሆኑ ወርቅይታደስ አበበ በሁለት ጎሎች ተሳትፎ (አንድ አስቆጥሮ አንድ በማመቻቸት) ያለው ተጫዋች ሆኗል።

– ኦሴ ማውሊ በሊጉ በተከታታይ ጨዋታ ጎል ያስቆጠረ ብቸኛው ተጫዋች ነው።

– የአዳማ ከተማው ዳዋ ሆቴሳ በውድድር ዓመቱ ከቀጥታ የቅጣት ምት ጎል ያስቆጠረ የመጀመርያው ተጫዋች ሆኗል። አጥቂው ባለፈው የውድድር ዓመትም በአንደኛው ሳምንት ወላይታ ድቻ ላይ በማስቆጠር የመጀመርያው ተጫዋች እንደነበር አይዘነጋም።

– ባህር ዳር ከተማ፣ መከላከያ እና ሲዳማ ቡና በሁለቱ ጨዋታዎች ጎል ያላስተናገዱ ብቸኞቹ ቡድኖች ናቸው።

– ጅማ አባ ጅፋር እና ሰበታ ከተማ እስካሁን ጎል ያላስቆጠሩ ቡድኖች ናቸው።

ዲሲፕሊን

– በዚህ ሳምንት በተደረጉ ስምንት ጨዋታዎች 38 ተጫዋቾች እና አንድ አሰልጣኝ (ፀጋዬ ኪዳነማርያም) የማስጠንቀቂያ ካርድ ተመዟል። በቢጫ ከርድ ረገድ የተመዘገበው ቁጥርም ካለፈው ሳምንት ጋር ተመሳሳይ ሆኗል።

– ባለፈው ሳምንት አራት ተጫዋቾች ቀይ ካርድ የተመለከቱበት ሊግ በዚህ ሳምንት ምንም ሳይመዘገብበት ተጠናቋል።

– ወላይታ ድቻ በስድስት ተጫዋቾችቹ እና በዋና አሰልጣኙ በድምሩ 7 የማስጠንቀቂያ ካርድ በማስመዝገብ ከፍተኛውን ቁጥር ሲይዝ አርባምንጭ፣ ባህር ዳር ከተማ፣ መከላከያ፣ ሲዳማ ቡና፣ ድሬዳዋ ከተማ እና ጅማ አባጅፋር አንድ አንድ ተጫዋች ብቻ ቢጫ ካርድ በማስመዝገብ ዝቅተኛውን ያስመዘገቡ ሆነዋል።

የሳምንቱ ስታቶች
(መረጃዎቹ የተገኙት ከሱፐር ስፖርት ነው)

ኢላማ የጠበቀ ሙከራ

ከፍተኛ – ሲዳማ ቡና እና አርባምንጭ (5)
ዝቅተኛ – ሀዲያ ሆሳዕና (0)

ጥፋት

ከፍተኛ – ቅዱስ ጊዮርጊስ (27)
ዝቅተኛ – ፋሲል ከነማ (9)

ከጨዋታ ውጪ

ከፍተኛ – ባህር ዳር ከተማ (7)
ዝቅተኛ – አርባምንጭ፣ ፋሲል እና ሆሳዕና (1)

የማዕዘን ምት

ከፍተኛ – ሰበታ ከተማ (7)
ዝቅተኛ – ሀዲያ ሆሳዕና (0)

የኳስ ቁጥጥር

ከፍተኛ – ኢትዮጵያ ቡና (69%)
ዝቅተኛ – ቅዱስ ጊዮርጊስ (31%)