ሀዲያ ሆሳዕና በፍርድ ቤት ዕግድ ተላለፈበት

ከዓምናው ያደረው የክለቡ እና የተጫዋቾቹ ውዝግብ ወደ መደበኛ ፍርድ ቤት አምርቶ ብይን አግኝቷል።

የክለቡ ተጫዋቾች የነበሩት አክሊሉ ዋለልኝ፣ ሱሌይማን ሀሚድ፣ አማኑኤል ጎበና እና ብሩክ ቀልቦሬ “ሊከፈለን የሚገባ በድምሩ ሁለት ሚሊዮን ብር ሀድያ ሆሳዕና ሊከፍለን አልቻለም። ” በሚል በህግ አማካሪው አቶ ብርሀኑ በጋሻውን አማካኝነት በመደበኛ ፍርድ ቤት ክሳቸውን ሲከታተሉ ቆይተዋል።

ጉዳዩን ሲመለከት የነበረው የልደታ ምድብ 5ኛ ፍ/ብሔር ችሎት ሀዲያ ሆሳዕና ከሊግ ካምፓኒው ከሚያገኘው ገቢ ሁለት ሚሊየን ብር ብቻ ታግዶ እንዲቆይ ትዕዛዝ በመስጠት ቀጣይ ቀነ ቀጠሮ ለህዳር አስራ አራት መስጠቱን አረጋግጠናል።

የእግድ ደብዳቤውንም የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን ለሊግ ካምፓኒው ያደረሰው መሆኑ ሲታወቅ ቀጣይ የፍርድ ቤት ሂደቱ የሚጠበቅ ይሆናል።