ሴቶች ፕሪምየር ሊግ | አዲስ አበባ ከተማ የሁለት ተጫዋቾችን ዝውውር አጠናቋል

በአሰልጣኝ የሺሃረግ ለገሰ የሚመራው የመዲናይቱ የእንስቶች ቡድን ተጨማሪ ሁለት አዳዲስ ተጫዋቾችን በዛሬው ዕለት አጠናቋል፡፡

በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪምየር ሊግ አንደኛ ዲቪዚዮን ላይ የሚወዳደረው አዲስ አበባ ከተማ በተጠናቀቀው የውድድር ዓመት የመጨረሻ የሊጉ ሳምንታት በጊዜያዊ አሰልጣኝነት ስትመራ የነበረችሁን የሺሃረግ ለገሰን በዋና አሰልጣኝነት በክረምቱ ከቀጠረ በኋላ ዘጠኝ አዳዲስ ተጫዋቾችን ያስፈረመ ሲሆን አስራ ሶስት ነባር ተጫዋቾችን ከወራት በፊት ውላቸውን ማደሱ ይታወሳል፡፡

ለዚህ ዓመት የፕሪምየር ሊጉ ጉዞው ልምምድ ከጀመረ የሰነባበተው ክለቡ በኢትዮጵያ ወጣቶች እና ስፖርት አካዳሚ ላለፉት አራት ዓመታት በስልጠና የቆየችሁ እና በቅርቡ በሴካፋ ከ20 አመት በታች ዋንጫ ሀገሯን ወክላ በመጫወት ጥሩ ቆይታ የነበራት አጥቂዋ አርያት ኦዶንግ እና የአቃቂ ቃሊቲዋ የመስመር አጥቂ ያብስራ ይታየው በይፋ የመዲናቱን ክለቡ ተቀላቅለዋል፡፡