በኢትዮጵያ ቡና እና ታፈሰ ሰለሞን ዙርያ አዲስ ነገር ተሰምቷል

ኢትዮጵያ ቡና የወራት ደሞዙ ላይ ቅጣት ቢያስተላልፍበትም ታቃውሞ ባሰማው ታፈሰ ሰለሞን ዙርያ ወቅታዊ መረጃ እናጋራችሁ።

ከቀናት በፊት ታፈሰ ሰለሞን ልምምድ ቦታ አለመገኘቱን ተከትሎ በቡድን መሪው አማካኝነት በቀረበው ሪፖርት መሠረት የወራት ደሞዙ እዳይከፈለው ውሳኔ መወሰኑ ይታወቃል። ይህን ውሳኔ ተቃውሞ ደብዳቤውን ያልተቀበለው ታፈሰ ሰለሞን በአንፃሩ የመልቀቂያ ደብዳቤ ለማስገባት ዝግጅት ላይ መሆኑን ከዚህ ቀደም በነበረው ዘገባችን ገልፀን ነበር።

አሁን ባለው አዲስ መረጃ መሠረት የክለቡ ሥራ አስኪያጅ አቶ ገዛኸኝ ወልዴ እና ታፈሰ ሰለሞን ረፋድ ላይ ቢሮ ተገናኝተው የተነጋገሩ ሲሆን በዋናነት በተጫዋቹ እና በክለቡ መካከል መግባባት ላይ ተደርሶ ታፈሰ ሰለሞን ነገ ወደ ሀዋሳ በማቅናት ቡድኑን እንዲቀላቀል መስማማታቸው ታውቋል።

አሰልጣኝ ካሳዬ አራጌ ታፈሰን አስመልክቶ “በቀጣይ የምናገኝበት ሁኔታ ሊኖር ይችላል” በማለት ከጅማ አባ ጅፋር ጨዋታ መጠናቀቅ በኃላ መናገራቸው ይታወሳል።