ባህር ዳር ከተማ ቅሬታውን ለሊግ ካምፓኒው አቅርቧል

በትናንት ምሽቱ ጨዋታ በረከት ደስታ በሁለተኛ ቢጫ ካርድ ከሜዳ መውጣት ነበረበት ሲል ባህር ዳር ከተማ አመልክቷል።

በቤትኪንግ ኢትዮጵያ ፕሪሚየት ሊግ ሰባተኛ ሳምንት ትናንት ማምሻውን ባህር ዳር ከተማ እና ፋሲል ከነማ ያደረጉት ጨዋታ ያለግብ መጠናቀቁ የሚታወስ ነው። ከውጤቱ ባሻገር ግን ባህር ዳር ከተማ የዳኝነት ስህተት ተፈፅሟል ሲል ለሊግ ካምፓኒው ረፋዱን ባስገባው ደብዳቤ ቅሬታውን ገልጿል። በቅሬታውም በጨዋታው መገባደጃ ላይ ሲታዩ ከነበሩት ጉሽሚያዎች ውስጥ በአንደኛው ላይ ተሳትፎ የነበረው በረከት ደስታ በሁለተኛ ቢጫ ካርድ መውጣት ነበረበት የሚል ሆኗል።

እንደ ባህር ዳሮች ቅሬታ በ69ኛው ደቂቃ አለልኝ አዘነ ላይ ጥፋት ሰርቶ የመጀመሪያ ቢጫ ካርድ የተመለከተው ተጫዋቹ በ89ኛው ደቂቃ ላይ ሣለአምላክ ተገኘ የሰራበትን ጥፋት ተከትሎ በፈጠሩት ጉሽሚያ የዕለቱ አርቢትር ቢኒያም ወርቅአገኘሁ ለሁለቱም ተጫዋቾች ቢጫ ካርድ ማሳየታቸውን ተከትሎ በረከት ደስታ በሁለተኛ ቢጫ ካርድ መውጣት ነበረበት የሚል ነው።