የአሰልጣኞች አስተያየት | ሀዲያ ሆሳዕና 3-2 ድሬዳዋ ከተማ

እጅግ አወዛጋቢ የነበሩ የዳኝነት ውሳኔችን ከተመለከተንበት ጨዋታ መጠናቀቅ በኃላ የሁለቱ ቡድኖች አሰልጣኞች ተከታዩን ሀሳብ ሰጥተዋል።

ሙሉጌታ ምኅረት – ሀዲያ ሆሳዕና

ስለማጥቃት አፈፃፀማቸው

“ሊጉ በጣም ከባድ ነው ስትመራ እና ስትመራ ያለው ነገር በጣም የተለያየ ነው ስተመራ አስጠብቀህ ለመውጣት ትንቀሳቀሳለህ ስትመራ ደግሞ ነቅለህ ለማጥቃት ትሄዳለህ። ከሰራነው አንፃር ከሆነ አጨራረስ ላይ በጣም ስንሰራ ነበር የቆየነው ቢሆንም ግብ ሶስት ግብ አስቆጥረን ማሸነፋችን ጥሩ ነገር ነው።የሚቀሩ ነገሮች አሉ እነሱን በቀጣይ አሻሽለን ለመምጣት እንሞክራለን።”

ስለድሬዳዋ ከተማዎች የመጀመሪያ ፍፁም ቅጣት ምት

“በእርግጥ እኔ ምስሎችን አይቼ ነው ሀሳብ መስጠት የምፈልገው ዳኛው ቅርብ ቦታ ስላለ የዳኛውን ውሳኔ እቀበላለሁ ለዛም ነበር ተጫዋቾቼን ስመልስ የነበረው። አሁን ሳየው ግን ውጭ ነው የሚመስለው ነገር የዳኛን ውሳኔ እናከብራለን።”

በጨዋታው የሚፈልገውን ስለማግኘቱ

“አዲስ ቡድን እንደመሆኑ ሁሉ ነገር በአንዴ አይሄድልህም ከሞላ ጎደል ከሲቱ ካፑ ጀምሮ ያለው እድገት ደስተኛ ነኝ በሂደት ግን የምንፈልገው ነገር ይመጣል ብዬ አስባለሁ።”

ዘማርያም ወ/ጊዮርስ – ድሬዳዋ ከተማ

ስለ ዳንኤል ደምሴ መውጣት እና የሀዲያ ሁለተኛ ፍፁም ቅጣት ምት

“ሁለት ጊዜ መምራት ችለን ነበር ነገርግን የዳንኤል እና የእንየው አለመኖር ጎድቶናል ፤ እንደ ቡድን እንቅስቃሴያችን ጥሩ አልነበረም እንደዛም ሆኖ እድሎችን አግኝተን ነበር። ከርቀት ብሆንም ውስጤ ብዙም ደስተኛ አይደለም ይህን እንግዲህ በጣም ከባድ ነው ተመልካች የሚፈርደው ነው እኛ ቡድን ላይ ተደጋጋሚ መሰል ውሳኔዎች እየተሰጡብን ነው እኛ የመጀመሪያ ፍ/ቅ/ም ስናገኝ ከመደሰት ይልቅ እልል ሲሉ ነበር ለካ እኛም እናገኛለን ብለው ማለት ነው በተወሰነ መልኩ በስነልቦና ረገድ ውሳኔዎች ጫና እየፈጠሩብን ነው።”

በተከታታይ ጨዋተዎች ነጥብ ስለመጣላቸው

“ዛሬ አሸንፈን ቢሆን ኖሮ ከመሪዎቹ በአራት ነጥብ ርቀን የምንቀመጥበትን እድል እንፈጥር ነበር ፤ ከውጤት አንፃር ውድድሩ እየተጀመረ ስለሆነ ብዙም የሚያሰጋ አይደለም። ከእንቅስቃሴ አንፃር ግን ብዙ መሻሻሎች የሚገባቸው ነገሮች አሉ።”

በሁለተኛው አጋማሽ በማጥቃቱ ረገድ ስለመቀዛቀዛቸው

“በፈጣን መልሶ ማጥቃት የመጫወት ፍላጎት አለን ከመጀመሪያው አንፃር በሁለተኛው አጋማሽ የመውረድ ነገር ነበር ሁለቴ የመራ ቡድን ውጤቱን አስጠብቆ የመውጣት ነገር እንመለከት ነበር።”