ዋልያው አምስት ተጫዋቾችን እና ሦስት የአሠልጣኝ ቡድን አባላቱን ዛሬ አያገኝም

ምሽት 12:30 ከሱዳን አቻው ጋር የአቋም መፈተሻ ጨዋታ የሚያደርገው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን አምስት ተጫዋቾችን እና ሦስት የአሠልጣኝ ቡድን አባላቱን በጨዋታው እንደማያገኝ ሶከር ኢትዮጵያ አረጋግጣለች።

በካሜሩኑ አስተናጋጅነት በሚከናወነው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ የሚሳተፈው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ከቀናት በፊት ወደ ስፍራው በማቅናት ልምምዱን እያከናወነ እንደሆነ ይታወቃል። ብሔራዊ ቡድኑም በዛሬው ዕለት የመጀመሪያ የአቋም መፈተሻ ጨዋታውን ከሱዳን አቻው ጋር ከደቂቃዎች በፊት የሚያከናውን ይሆናል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ ብሔራዊ ቡድኑ በኮቪድ-19 ምክንያት አምስት ተጫዋቾችን እና ሦስት የአሠልጣኝ ቡድን አባላቱን በጨዋታው እንደማያገኝ ሶከር ኢትዮጵያ ከምንጮቿ አረጋግጣለች። ለተጫዋቾቹ እና አሠልጣኞቹ የግል መብት ስንል ስማቸውን ከመጥቀስ ብንቆጠብም ግለሰቦቹ በአሁኑ ሰዓት ራሳቸውን አግለው እንደሚገኙም ለማወቅ ችላናል።

በጉዳዩ ላይ የሚኖሩ አዳዲስ ነገሮችን እየተከታተልን የምናቀርብ ይሆናል።