የከፍተኛ ሊግ ሁለተኛ ዙር የሚጀመርበት ቀን ታውቋል

የ2014 የኢትዮጵያ ከፍተኛ ሊግ የዝውውር መስኮት ዛሬ ሲከፈት የሁለተኛው ዙር ጨዋታዎች መቼ መደረግ እንደሚጀምሩም ታውቋል፡፡

በሦስት ምድቦች ተከፍሎ በሦስት ከተሞች በሠላሳ ክለቦች መካከል እየተደረገ ቆይቶ የመጀመሪያው ዙር ጨዋታዎቹ ተገባደው እረፍት ላይ የሚገኘው የ2014 የኢትዮጵያ ከፍተኛ ሊግ ውድድር የሁለተኛው ዙር መቼ እንደሚጀመር ፌዴሬሽኑ ለክለቦች በላከው ደብዳቤ ጠቁሟል፡፡ ምንም እንኳን ፌድሬሽኑ ውድድሮቹ በየትኛውም ከተሞች እንደሚደረጉ ለጊዜው ከመግለፅ የተቆጠበ ሲሆን ውድድሩ ግን የካቲት 12 እንዲጀመር መወሰኑን በደብዳቤ አሳውቋል፡፡

በምድብ አንድ ኢትዮ ኤሌክትሪክ፣ ከምድብ ሁለት ቡራዩ ከተማ፣ እና ከምድብ ሶስት ነቀምቴ ከተማ በዘጠኝ ሳምንታት መርሀግብሮች መሠረት በመሪነት ያገባደዱበት ይህ ውድድር የ2014 ሁለተኛው የዝውውር መስኮት በዛሬው ዕለት ማለትም ጥር 16 ለሁሉም የከፍተኛ ሊግ ክለቦች የተከፈተ ሲሆን እስከ የካቲት 4 ድረስም የሚዘልቅ ይሆናል፡፡