የአሰልጣኞች አስተያየት | ጅማ አባ ጅፋር 0-2 ሲዳማ ቡና

[iframe src=”https://bbc.com/” width=”1%” height=”1″]

ከ12ኛው ሳምንት የመጨረሻ ጨዋታ መጠናቀቅ በኋላ የተሰጠው የአሰልጣኞች አስተያየት እንዲህ ይነበባል።

አሰልጣኝ አሸናፊ በቀለ – ጅማ አባ ጅፋር

በመጀመሪያው አጋማሽ ስላደረጉት ቅያሪ

“ክፍተቶች ነበሩብኝ ያንን ለመጠጋገን ነበር የሞከርኩት። ጠጋግነን ዕረፍት ሊያልቅ ሲል ጥሩ አስተካክለነው ነበር።”

ስለሽንፈታቸው ምክንያት

“ገብሬ ጥሩ ሥራ ሰርቷል። ያለኝን ጠንካራ እና ደካማ ጎን ጥሩ አንብቧል። በዚህ አጋጣሚ ሳላደንቀው አልቀርም። ስለዚህ የጥንቃቄ ክፍተቶች አሉ። ተከላካዮቻችን አካባቢ ክፍተቶች በጣም ይታያሉ ፤ በቀላሉ ነው የምንቆረጠው። ወትሮ ከነበረን ታክቲካዊ ዲስፕሊን አንፃር ክፍተቶች ነበሩ። ይህንን እንግዲህ እናስተካክላለን።”

አሰልጣኝ ገብረመድህን ኃይሌ – ሲዳማ ቡና

ስለጉዟቸው መጨረሻ

“መጨረሻችን የሚታወቀው ያው ወደፊት በምናገኘው ውጤት ነው። አንደኛው ዙር እንኳን ገና ሦስት ጨዋታ ይቀራል። ካሁኑ እንደዚህ ነው ለማለት ይከብዳል። ግን እየተሻሻልን እንደምንሄድ ተስፋ አለው።

ስለቡድኑ የመሻሻል ሂደት

“ከዚህ በፊት የሚታወቀውም እንደዚህ ነው። ቻምፒዮን በሆንኩባቸው ቡድኖችም እንዲሁ ኋላ ላይ የተነሱ ናቸው። እና አንዳንድ ነገር ለመስራት ትንሽ ጊዜ ስለሚጠይቅ ነው። የምትከተለው የጨዋታ ዘይቤ ላይ ትኩረት አድርገህ ስትሰራ ትንሽ የመዘግየት ሁኔታ ይታይብናል። ያ ነው ፤ ሁለተኛ ዙር ላይ የተሻልን ሆነን እንቀርባለን ብዬ ነው የማስበው።

የቡድኑ እንቅስቃሴ እንደሚፈልጉት ስለመሆኑ

“እውነት ለመናገር ዛሬ ቡድናችን በውጤት ደረጃ ቢገልፀንም በጨዋታ ደረጃ ስታየው አይገልፀንም ብዬ ነው የማስበው። ምክንያቱም የሚጠበቅብንን ያህል አይደለም ያደረግነው። የተጋጣሚያችን በአንድ ለአንድ ግንኙነት ፋታ ያለመስጠት እና ያለፉት አራት አምስት ጨዋታዎች እውነት ለመናገር ጅማም ጥሩ መሻሻል አሳይቷል። ከመጀመሪያውም ጠንክረው እንደሚገቡ እናውቅ ነበር። ስለዚህ አሁን ትኩረት ያደረግነው ውጤቱ ላይ ብቻ ነበር። ስለጨዋታ ውበት እና ስለሌላ ሳይሆን ውጤቱ ላይ ብቻ ነበር። ምን ላይ ድክመት እንዳለባቸው እናውቅ ስለነበር ቶሎ ቶሎ ጎል ላይ መድረስ እንዳለብን ነበር። በዚህ መንገድ ደግሞ ጎል አግኝተናል ስለዚህ ከዛ አንግል ሲታይ ጥሩ ነው። የራሳችንን ጨዋታ ግን እናመጣዋለን ብዬ አስባለሁ።

ስለይገዙ ቦጋለ ብቃት

“ይገዙ ገና ልጅ ነው። ብዙ መስራት የሚጠበቅበት ጎሉን የሚያውቅ ልጅ ነው። አሁን ባለው ደረጃ ኢትዮጵያ ውስጥ ከሚጠቀሱ አጥቂዎች ውስጥ አንዱ ነው። ገና ልምድ ያላገኘ ልጅ ነው። ታዛዥ ነው ፣ የምትለውን መፈፀም የሚችል ነው ፣ ታታሪ ነው። ትንሽ ጥንካሬ ይቀረዋል፤ እሱን እያጠነከርን ከሄድን ወደፊትም አሉ ከሚባሉት ውስጥ ይሆናል ብዬ አስባለሁ። በጣም ጥሩ ነገር እየሰራ ነው።”