ከ17 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድን ረዳት አሰልጣኞች ታውቀዋል

[iframe src=”https://bbc.com/” width=”1%” height=”1″]

በህንድ ለሚዘጋጀው የሴቶች ከ17 ዓመት በታች ዓለም ዋንጫ የቅድመ ማጣሪያ ያለበት የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ረዳት አሰልጣኞች ተለይተዋል፡፡

ከሰሞኑ በህንድ አስተናጋጅነት በሚደረገው ከ17 ዓመት በታች ሴቶች ዓለም ዋንጫ በአፍሪካ ዞን የማጣሪያ መርሐግብር ከዩጋንዳ አቻው ጋር ጨዋታ ያለበት የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድን አሰልጣኝ እንዳልካቸው ጫካን በዋና አሰልጣኝ የመረጠ ሲሆን አሰልጣኙም ከትላንት በስቲያ ለ44 ተጫዋቾች ጥሪ በማድረግ በያዝነው ሳምንት ወደ ቅድመ ዝግጅት እንደሚገቡ ታውቋል። አሁን ደግሞ የአሰልጣኝ እንዳልካቸው ረዳቶችም ታውቀዋል፡፡

በዚህም መሠረት ረጅም ዓመታትን በሴቶች እግር ኳስ አሰልጣኝነት የምናውቀው የቀድሞው የኢትዮ ኤሌክትሪክ እና እንዲሁም ከዚህ ቀደም የኢትዮጵያ ሴቶች ከ20 አመት በታች ብሔራዊ ቡድን ዋና አሰልጣኝ የነበረው ቴዎድሮስ ደስታ እና በአሁኑ ሰአት የኢትዮጵያ ወጣቶች እና ስፖርት አካዳሚ የሴቶች እንዲሁም ከዚህ ቀደም የወንድ ቡድን አሰልጣኝ በመሆን አሁንም ድረስ እያገለገለ የሚገኘው ኩመራ በቀለ በረዳት አሰልጣኝነት ተሹመዋል። በኢትዮጵያ ቡና ፣ ሀዋሳ ከተማ እንዲሁም የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ግብ ጠባቂ በመሆን ከዚህ ቀደም ያገለገለው እና ወደ ሥልጠናው በመግባት የሳዳት እና ከማል አካዳሚን በመመስረት አሰልጣኝ ሆኖ እየሰራ የሚገኘው ሳዳት ጀማል የብሔራዊ ቡድኑ የግብ ጠባቂ አሰልጣኝ በመሆን ስለመመረጣቸው ሶከር ኢትዮጵያ አውቃለች፡፡