ከፍተኛ ሊግ | ሀምበሪቾ አዲስ አሰልጣኝ ሾሟል

[iframe src=”https://bbc.com/” width=”1%” height=”1″]

አሰልጣኝ ደጉ ዱባሞ የሀምበሪቾ ዱራሜ አዲሱ አሰልጣኝ ሆኗል፡፡

በኢትዮጵያ ከፍተኛ ሊግ ምድብ ሐ ስር የሚገኘው እና በመጀመሪያው ዙር የከፍተኛ ሊግ ውድድር ደካማ ጊዜን ያሳለፈው ሀምበሪቾ ዱራሜ ከዳዊት ሀብታሙ ጋር ከተለያየ በኋላ አሰልጣኝ ተመስገን ዳናን ለመቅጠር ሁሉንም ነገር አጠናቆ የነበረ ቢሆንም አሰልጣኙ ወልቂጤ ከተማን ምርጫቸው በማድረጋቸው የተነሳ ክለቡ ፊቱን ወደ አዲስ አሰልጣኝ አዙሯል፡፡

አሰልጣኝ ደጉ ዱባሞ አዲሱ የክለቡ አሰልጣኝ ሆኖ ተሹሟል፡፡ በእግር ኳስ ተጫዋችነት በስድስት ክለቦች ተጫውቶ ያለፈው እና ወደ አሰልጣኝነቱ ከገባ በኋላ በመተሀራ እና አካባቢዋ በርካታ ተጫዋቾችን በማሰልጠን የአሰልጣኝነት ህይወቱን የጀመረ ሲሆን አሰልጣኙ የክለብን ህይወትንም የመተሀራ ቡድንን በመያዝ እስከ 2009 ድረስ ቆይታን አድርጓል፡፡

በመቀጠል ከ2010 እስከ ተጠናቀቀው የውድድር ዓመት ድረስ በአዳማ ከተማ ረዳት እንዲሁም ጊዜያዊ አሰልጣኝ ሆኖ ሲያገለግል የነበረ ሲሆን እስከ ዓመቱ መጠናቀቂያ ድረስ ሀምበሪቾ ዱራሜን በመረከብ በዛሬው ዕለት ከአቃቂ ቃሊቲ ጋር በተደረገው የሁለተኛ ዙር መርሀግብር በይፋ ስራ ጀምረዋል።