​የአሠልጣኞች አስተያየት | ሲዳማ ቡና 1-0 አዲስ አበባ ከተማ

[iframe src=”https://bbc.com/” width=”1%” height=”1″]

በሲዳማ ቡና አሸናፊነት ፍፃሜውን ካገኘው ጨዋታ በኋላ አሠልጣኞች ተከታዩን የድህረ-ጨዋታ አስተያየት ሰጥተዋል።

ገብረመድህን ኃይሌ – ሲዳማ ቡና

ጨዋታው እንዴት ነበር?

ደህና ነው ፤ መጥፎ አይደለም። ከውጤት አንፃር ጥሩ ነው። አሁንም ግን ማሻሻል የሚገባን ነገር አለ። የምንስታቸው ኳሶች አሉ። እነሱ ዋጋ ሊያስከፍሉን ስለሚችሉ ማሻሻል የሚገባን ነገር ነው። ግን ወደ አሸናፊነት መመለሳችን ለሚቀጥሉት ጨዋታዎች ጥሩ ነው።

አሁን አራተኛ ደረጃ ስለመድረሳቸው እና ስለ ቀጣይ…?

አይታወቅም ፤ ገና ዳዴ እያልን ነው ማለት ይቻላል። ዋናው አራተኛ መድረሱ ሁለተኛ አንደኛ መድረሱ አይደለም። ከመሪዎቹ ጋር መጠጋት ነው አስፈላጊ። ያለበለዚያ ደረጃውም መውረዱ አይቀርም።

ደምሰው ፍቃዱ – አዲስ አበባ ከተማ

ቡድኑ ተዳክሞ ስለታየበት ምክንያት?

ወጥ የመሆን ነገር ይጎለናል። የምንችለውን ሞክረናል። በእንደዚህ ዓይነት ከቀጠልን ጥሩ ስላልሆነ ይሄንን ለመቅረፍ ሙከራ እናደርጋለን። 

ሜዳ ላይ የነበረው ክፍተት ምን ነበር?

መሐል ሜዳ ላይ የሚጫወቱት ተጫዋቾች ጥሩ አለመሆን ዳር እና ዳር እንዲሁም የመሐል አጥቂዎቻችንን መጠቀም አልቻልንም። የተፈጠሩ አጋጣሚዎች ነበሩ። እነዛን አጋጣሚዎች የመጠቀም ጉዳይ አለ። ግን ብዙ ጊዜ ኳሶች ከመሐል ጥሩ በሆኑ ጊዜ ዳር እና ዳር ውጤታማ ይኮናል። በኳስ የሞከራል ሊሳት ይችላል። የተገኙትን አጋጣሚዎች ለመጠቀም ግን ከዚህ ስለሚነሱ የተሻለ ነገር ለማስመዝገብ የግድ መስራት ይኖርብናል።

ስለተጋጣሚ ቡድን አቀራረብ?

ተጋጣሚያችን ትልቅ ቡድን ነው። ግን ደግሞ በጣም ቀዝቀዝ ብለው ነበር የቀረቡት። ምናልባት ወደእነርሱ የአጨዋወት ፍላጎት ላይ መግባታችን ተፅዕኖ አሳርፎብናል።