የአሰልጣኞች አስተያየት | ወላይታ ድቻ 1-0 ሀዲያ ሆሳዕና

[iframe src=”https://bbc.com/” width=”1%” height=”1″]

የጨዋታ ሳምንቱ የመጨረሻ ከነበረው ጨዋታ መጠናቀቅ በኃላ የሁለቱ ቡድኖች አሰልጣኞች ተከታዩን ሀሳብ ሰጥተዋል።

ፀጋዬ ኪዳነማርያም – ወላይታ ድቻ

መከላከልን ስለመምረጣቸው

“ወሳኝ ሦስት ነጥብ በማሳካትችን በጣም ደስተኛ ነኝ። ተጫዋቾቼም ላሳዩት ጥረት ላመሰግናቸው እወዳለሁ። እግርኳስ እንዲህ እየተከላከልክ ታጠቃለህ፤ እያጠቃህም ትከላከላለህ። እነዚህን መርሆዎች ነው እኔ የምከተለው። አስቀድመን እንዳሰብነው በምንይሉ እና ስንታየሁ ለማጥቃት ፈልገን ነበር። ነገርግን ከተጋጣሚያችን ሁኔታ አንፃር ይህን ለመተግበር ተቸግረናል። ያንን በሂደት ለማስተካከል ሞክረናል። ግቧን ካስቆጠርን በኃላ ይበልጥ ታክቲካሊ ዲሲፕሊንድ ሆነን ተጫውተናል። ሦስት ነጥብ ያስገኝልናል ባልነው መንገድ የእነሱን አጥቂዎች እንቅስቃሴ ገድበን ውጤታማ መሆን ችለናል።”

ስለቡድኑ የማሸነፍያ ቀመር

“ቡድናችን ባሉን ልጆች ለመጠቀም እየሞከርን ነው። ልጆቻችን ሁለገብ ሚናን መወጣት የሚችሉ ናቸው። የእኛ ቡድን ትልቁ ነገሩ፤ በጣም ፍላጎት ያላቸው ልጆች ናቸው። ደጋፊው ከውጭ ሆኖ በፀሎት ከጎናችን ነው አመራሩ ይደግፈናል። እኔም ቡድኑ ጥሩ ቦታ ደርሰው እንዲያዩ ጠንክሬ እየሰራሁ እገኛለሁ። የዚህ ሁሉ ድምር ውጤት ከመሪዎቹ ጋር በቅርብ ርቀት እንድንገኝ አስችሎናል።

ሙሉጌታ ምህረት – ሀዲያ ሆሳዕና

ስለጨዋታው

“ሲጀመር አስቀድመው ግብ ካስቆጠሩብን ይህ እንደሚሆን አውቀን ነበር ጥንቃቄም ለማድረግ ሞክረን ነበር ነገርግን በራሳችን ስህተት ግብ ተቆጥሮብን ተሸንፈናል።ልጆቼ ያደረጉት ተጋድሎ ጥሩ ነበር ክፍተቶች ቢኖሩብንም የሚታዩ ነገሮች አሉን እነሱን አሻሽለን በቀጣይ ለመቅረብ እንሞክራለን።”

ቡድኑ ሁለተኛ እቅድ ስላለመኖሩ

“ጥቅጥቅ ብለው ግማሹን ሜዳ ይዘውት ነበር ይህን ለማስከፈት ሞክረናል ነገርግን ያንን ለማስከፈት ትዕግሥት ስላልነበረን ውጤቱን ልናጣ ችለናል።”

በጨዋታው ያልነበሩ ተጫዋቾች ስለፈጠሩት ተፅዕኖ

“ቢኖሩ ጥሩ ነው ነገርግን ሌሎቹ ደግሞ መጫወት ስላለባቸው ተጠቅመናቸዋል ነገም ሌሎች ላይኖሩ ስለሚችሉ የምንጠቀምባቸው በእነዚህ ስለሆነ መጥፎ ነገር አላየሁባቸውም ጥሩ ነው ከጨዋታ ርቀው የነበሩ እንዲሁም ቋሚም የነበሩ ልጆችም ስለሆኑ ተጠቅመናቸዋል ፤ 30 ልጆች የያዝነው ሊጫወቱ ስለሆነ አለመኖራቸው ሌሎች ተጫዋቾችን እንድናይ እድል ሰጥቶናል።”