የአሠልጣኞች አስተያየት | አርባምንጭ ከተማ 1-1 ሰበታ ከተማ

[iframe src=”https://bbc.com/” width=”1%” height=”1″]

አንድ ነጥብ ለሁለት የተጋሩት ሰበታ እና አርባምንጭ ከጨዋታው በኋላ በአሠልጣኞቻቸው ተከታዩን አስተያየት ሰጥተዋል።

መሳይ ተፈሪ – አርባምንጭ ከተማ

በሁለተኛው አጋማሽ ስላሳዩት ደካማ እንቅስቃሴ?

አንዳንዴ ፍላጎቶች የተሳሳተ ነገር ላይ ይወስዳሉ። ወደ ኋላ ስለሸሸህ የምታስጠብቅ ሊመስልህ ይችላል። የተጋጣሚ ቡድን ደግሞ ደግሞ ከተቆጠረበት በኋላ ነቅሎ የመምጣት እና ጫና የመፍጠር ነገር አለ። በመጀመሪያዎቹ ደቂቃዎች ጫና ፈጥረን በመጫወት የጎል አጋጣሚዎችን ስንፈጥር ነበር። ከዛ ከእረፍት በኋላ የነበረን እንቅስቃሴ ግን ጥሩ አይደለም።

የመጀመሪያው ዙር እንዴት አለፈ?

ጥሩም ጎኖች አሉ። ደካማም ጎኖች አሉት። እነዛን ጥሩ ነገሮች በደንብ እናስቀጥላለን። ክፍተቶች የነበሩብንን ደግሞ አርመን እንመጣለን።

የቡድኑ ፍጥነታዊ አጨዋወት ዛሬ ስለመቀነሱ?

ከሜዳው ጋር ተያይዞ ተጋጣሚ ቡድን ይዞት የሚመጣው አጨዋወቶች ይኖራሉ። ከጭቃው ጋር ተያይዞ። እኛ በከፍተኛ ግለት ነው የምንጫወተው። እንደዚሁም የአየር ኳስ ላይም ጠንካራ ነገር አለ። ግን ከዚህ ጋር ተያይዞ ያንን ነገር ላናይ እንችላለን።

ብርሃን ደበሌ – ሰበታ ከተማ (ጊዜያዊ አሠልጣኝ)

በሁለቱ አጋማሽ ጨዋታውን ስለቀረቡበት መንገድ?

በመጀመሪያው አጋማሽ ለማድረግ ያሰብነውን እንቅስቃሴ ሜዳ ላይ ተመልክታችኋል። በሁለተኛው አጋማሽ ደግሞ የግድ ጎል ስለገባብን ማግባት ስላለብን ተጭነን ለመጫወት ሞክረናል። ተሳክቶልንም አንድ ጎል አስቆጥረናል። ሌሎች ግቦችንም ለማስቆጠር ጥረት እያደረግን ነበር።

በመጀመሪያው ዙር ስለነበራቸው ደካማ እንቅስቃሴ እና በሁለተኛው ዙር ሊያደርጓቸው ስለሚችሉት ለውጥ?

በመጀመሪያዎቹ 15 ጨዋታዎች 5 ተከታታይ ሽንፈቶችም አጋጥሞን ነበር። በዛን ወቅት እኔ አልነበርኩም። ቢሆንም ግን ሰበብ መስጠት ሳይሆን ያንን ለማካላስ የሚወጡትን ተጫዋቾችን አሶጥተን የሚገቡትን አስገብተን በሁለተኛው ዙር የተሻለ ለማድረግ እንሰራለን ብዬ አስባለው።

ቡድኑ ላይ ስላለው ችግር?

ውስብስብ ነገሮች ሊኖሩ ይችላሉ።

ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች ቡድኑ ላይ ስለታየው መነሳሳት?

እኔ ለመስራት የሚከርኩት አምሮዋቸው ውስጥ የነበረውን ጭንቀት ለማውጣት ነው። የእግርኳስን ፅንሰ ሀሳብ ተከትለው እንዲንቀሳቀሱ ነው ስብሰባም ያደረግነው። ችግሮች የትኛውም ክለብ ላይ ሊኖሩ ይችላሉ። እኛም ክለብ ላይ ሊኖር ይችላል። ግን ያንን ነገር ረስተው ወደ ጨዋታቸው እንዲያተኩሩ ለማድረግ ነው። የተደረጉት ስብሰባዎችም ሙያዊ ናቸው።