በዓምላክ ተሰማ ከፍተኛ ግምት የተሰጣቸው ሁለት ጨዋታዎችን ይመራል

[iframe src=”https://bbc.com/” width=”1%” height=”1″]

በአህጉራዊ እና ዓለም አቀፋዊ ውድድሮች በርካታ ጨዋታዎችን የመራው ኢትዮጵያዊው አርቢትር ሁለት ተጠባቂ ጨዋታዎችን እንዲመራ ተመድቧል።

በአፍሪካ ከሚገኙ ምርጥ የመሐል ዳኞች መካከል አንዱ የሆነው በዓምላክ ተሰማ በካሜሩን አስተናጋጅነት በተከናወነው 33ኛው የአህጉሪቱ ውድድር አስደናቂ ብቃት በማሳየት ከብዙዎች አድናቆት ሲቸረው እንደነበር አይዘነጋም። የ41 ዓመቱ አርቢትር አሁንም ትልቅ ግምት የሚሰጣቸው ጨዋታዎችን መምራት ቀጥሎ የፊታችን ቅዳሜ እና መጋቢት 16 የሚደረጉትን ሁለት ተጠባቂ ጨዋታዎችን በመሐል አልቢትርነት እንዲከውን መመደቡን ሶከር ኢትዮጵያ አረጋግጣለች።

ቅዳሜ የሚደረገው ጨዋታ የአፍሪካ ቻምፒየንስ ሊግ ውድድር ሲሆን ተፋላሚዎቹም ማሜሎዲ ሰንዳውንስ እና አል አህሊ ናቸው። ደቡብ አፍሪካ ላይ የሚደረገውን ይህንን ጨዋታ ለመምራት አልቢትሩ ነገ ወደ ስፍራው እንደሚያመራም ሰምተናል።

መጋቢት 16 የሚደረገው ሁለተኛ ጨዋታ ደግሞ በኳታሩ ዓለም ዋንጫ አፍሪካን የሚወክሉ አምስት ቡድኖችን ከሚለዩ መርሐ-ግብሮች መካከል አንዱ ነው። እሱም ባማኮ ላይ ማሊ እና ቱኒዚያ የሚያደርጉት የመጨረሻ ዙር የመጀመሪያ መርሐ-ግብር ነው።