የዋልያዎቹ ተጋጣሚ ልምምድ ጀምሯል

[iframe src=”https://bbc.com/” width=”1%” height=”1″]

የፊታችን ዓርብ ከኢትዮጵያ ጋር የአቋም መፈተሻ ጨዋታ የሚያደርገው የኮሞሮስ ብሔራዊ ቡድን ለጨዋታው ልምምዱን ዛሬ ጀምሯል።

ዓለም አቀፍ የብሔራዊ ቡድኖች የጨዋታ ወቅት ካለንበት ሳምንት አጋማሽ ጀምሮ ክፍት የሚሆን ሲሆን ብሔራዊ ቡድኖችም የማጣሪያ ጨዋታዎችን እና የአቋም መፈተሻ ጨዋታዎችን ለማድረግ እየተሰናዱ ይገኛል። በአሠልጣኝ ውበቱ አባተ እና ረዳቶቹ የሚመራው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድንም ከኮሞሮስ አቻው ጋር የአቋም መለኪያ ጨዋታ ከሜዳው ውጪ ለማድረግ ቀጠሮ በመያዝ ያለፉትን አራት ቀናት ጠንከር ያለ ልምምድ እያከናወነ የሚገኝ ሲሆን ተጋጣሚውም በዛሬው ዕለት ዝግጅቱን ጀምሯል።

ከሁለት ሳምንታት በፊት የብሔራዊ ቡድኑ ዋና አሠልጣኝ ተደርገው የተሾሙት ዩነስ ዜርዱክ ከሦስት ቀናት በፊት ከኢትዮጵያ ጋር ለሚያደርጉት ጨዋታ ለ24 ተጫዋቾች ጥሪ ያቀረቡ ሲሆን በአብዛኛው ወጣት ተጫዋቾች ላይ ትኩረት እንዳደረጉም ተዘግቧል። ፍራንኮ-ሞሮኳን አሠልጣኙ ዛሬ ስብስባቸውን በተሟላ ሁኔታ ባያገኙም ጨዋታውን በሚያደርጉበት ስታድ ኦምኒስፖርትስ ማሉዚኒ ስታዲየም የመጀመሪያ ልምምድ ማሰራታቸው ታውቋል።