ብሔራዊ ቡድኑ የመጨረሻ ልምምዱን ሰርቷል

[iframe src=”https://bbc.com/” width=”1%” height=”1″]


የኢትዮጵያ ከ20 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ወደ ጋና ከሚያደርገው ጉዞ በፊት የሜዳ ላይ ዝግጅቱን አጠናቋል።

ለኮስታሪካው የ20 ዓመት በታች የሴቶች የዓለም ዋንጫ እየተደረገ በሚገኘው የማጣሪያ ውድድር የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን የመጨረሻው ምዕራፍ ላይ ደርሷል። ብሔራዊ ቡድኑ በማጣሪያው ማብቂያ ከጋና አቻው ጋር ተገናኝቶ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተደረገው የመጀመሪያ ጨዋታው 3-0 መሸነፉ አይዘነጋም። የዚሁ ጨዋታ የመልስ ፍልሚያ ደግሞ በመጪው እሁድ በጋና እንደሚደረግ ይጠበቃል።

ከ3-0ው ሽንፈት በኋላ ለሁለተኛው ጨዋታ ዝግጅቱን ማድረግ የቀጠለው የአሰልጣኝ ፍሬው ኃይለገብርኤል ስብስብ በዛሬው ዕለት ከረፋድ 04:00 ጀምሮ ቦሌ በሚገኘው የቅዱስ ጊዮርጊስ ሜዳ ከጉዞው በፊት የመጨረሻ የሆነው ልምምዱን አከናውኗል። በልምምዱ ላይ አሰልጣኝ ፍሬው ቀለል ያሉ ስራዎችን ሲያሰሩ ከቆዩ በኋላ የጋናውን ጨዋታ ማዕከል ያደረጉ የተጫዋቾቹን ታክቲካል ንቃት ከፍ ለማድረግ የሚረዱ ልምምዶችን ሰጥተዋል። ህመም ላይ ከምትገኘው ከቡድኑ ወሳኝ አጥቂ ረድኤት አስረሳኸኝ ውጪ ቀሪዎቹ የአሰልጣኝ ፍሬው ተመራጮች ልምምዳቸውን በጥሩ መንፈስ አከናውነው መጨረሳቸውን ታዝበናል።

ዛሬ ከሰዓት 09:00 ጀምሮ አሰልጣኙ በመጨረሻው የማጣሪያ ጨዋታ ዙሪያ በፌዴሬሽኑ ፅህፈት ቤት የሚሰጡት መግለጫም ይጠበቃል።