የጅማ አባ ጅፋር ተጫዋቾች ጥያቄ ምላሽ እያገኘ ነው

[iframe src=”https://bbc.com/” width=”1%” height=”1″]

ከቀናት በኋላ በአዳማ በሚጀምረው የሁለተኛው ዙር ውድድር ቅድመ ዝግጅታቸውን እስካሁን ያልጀመሩት የጅማ አባ ጅፋር ተጫዋቾች ጥያቄ አሁን ምላሽ ያገኘ ይመስላል።

የ2010 የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ አሸናፊው ጅማ አባ ጅፋር እግርኳስ ክለብ ለተከታታይ አራት ዓመታት የተጫዋቾች ደሞዝ በአግባቡ መክፈል ተስኖት በሚፈጠሩ ውዝግቦች የክለቡ ስም በበጎ እየተነሳ አይገኝም። ይህ ለዓመታት እየተንከባለለ የመጣው የቡድኑ መሠረታዊ ችግር ዘንድሮ አገርሽቶ ለወራት ያልተከፈለን ወርሐዊ ደሞዝ እስካልተከፈለን ድረስ አዳማ ለሚጀምረው የሁለተኛው ዙር ውድድር ቅድመ ዝግጅት አንጀምርም በማለት ተጫዋቾቹ አቋም በመያዛቸው ይህን ዘገባ እስካጠናቀርንት ጊዜ ድረስ ቡድኑ ተሰባስቦ ዝግጅት እንዳልጀመረ ይታወቃል።

ከሰሞኑን የቡድኑን ችግር በጊዛዊነት ለመፍታት ሲሯሯጥ የቆየው የክለቡ ቦርድአመራሮች በዛሬው ዕለት ለእያንዳንዳቸው ተጫዋች የሁለት ወር ደሞዝ እንደከፈላቸው አረጋግጠናል። የተጫዋቾቹ ጥያቄ ምላሽ ማግኘቱን ተከትሎ በባቱ ከተማ በሚካሄደው የከፍተኛ ሊግ የምድብ ለ ውድድሮችን በስታዲየም በመገኘት ጨዋታዎችን ሲከታተሉ የሰነበቱት አሰልጣኝ አሸናፊ በቀለ የቡድኑ አባላት በሙሉ ዛሬ አዳማ ከተማ በመግባት እንዲሰባሰቡ ጥሪ አቅርበዋል። ጥሪውን ተከትሎም ከነገ ጀምሮ መደበኛ ልምምዳቸውን ይጀምራሉ ተብሎ ይጠበቃል።

በሌላ ዜና በርከት ያሉ ቀሪ ኮንትራት ያላቸው የጅማ አባ ጅፋር ተጫዋቾች ከቡድኑ ጋር በስምምነት እንለያይ በማለት ደብዳቤ ማስገባታቸው ሲታወቅ የክለቡም አመራሮች ጉዳዩን እያጤኑት እንደሆነ ሰምተናል።