ድሬደዋ ከተማ ሁለት ተጫዋቾችን ከከፍተኛ ሊጉ አግኝቷል

አዲስ አሰልጣኝ የሾመው ድሬደዋ ከተማ በከፍተኛ ሊግ ውድድር ጎልተው መውጣት የቻሉ የመሐል ተከላካይ እና አማካይ ወደ ቡድኑ ቀላቅሏል።

ድሬደዋ ከተማን ለማሰልጠን የተረከቡት አሰልጣኝ ሳምሶም አየለ ከሄኖክ ኢሳያስ ጋር ከመለያየታቸው ውጭ ወደ ዝውውሩ በማግባት ተከላካይ አማረ በቀለን ማስፈረማቸው ይታወቃል። ዛሬ በከፍተኛ ሊጉ የተሳካ ጊዜ ያሳለፉ ሁለት ተጫዋቾችን ከንግድ ባንክ በውሰት አግኝተዋል።

የመሐል ተከላካይ ከድር ሀይረዲን እና አማካይ አባይነህ ፌኖ ለድሬደዋ ከተማ ግማሹን ዓመት ለማገልገል ክለቡ በደብዳቤ ባቀረበው የውሰት ጥያቄ መሰረት ዛሬ ፌዴሬሽን በመገኘት ውላቸውን ያሰፈሩ ሲሆን ረፋድ ላይ ቡድኑን የሚቀላቀሉ ይሆናል።

የመሐል ተከላካይ ከድር ሀይረዲን ከዚህ ቀደም በፋሲል ከነማ በጅማ አባ ጅፋር በሌሎችም ክለቦች ተጫውቶ ያሳለፈ ሲሆን ዘንድሮ ንግድ ባንክን በመቀላቀል ቡድኑን በአንበልነት እየመራ ጥሩ ጊዜን ማሳለፍ ችሏል።

አማካይ አባይነህ ፌኖ በወልቂጤ በሀዋሳ ከተማ በሌሎች ክለቦች ግልጋሎት ሲሰጥ ዘንድሮ ወደ ንግድ ባንክን ካመራ በኃላ የተሳካ ጊዜ ካሳለፉ ተጫዋቾች መካከል አንዱ ነው።