የአሰልጣኞች አስተያየት | መከላከያ 0-0 አርባምንጭ ከተማ

እምብዛም ማራኪ ካልነበረው እና በአቻ ውጤት ከተጠናቀቀው ጨዋታ መጠናቀቅ በኋላ የሁለቱ ቡድኖች አሰልጣኞች ተከታዩን ሀሳብ ሰጥተዋል።

አሰልጣኝ ዮሐንስ ሳህሌ – መከላከያ

ስለ ጨዋታው

“አራት አዳዲስ ተጫዋቾችን ለመጀመሪያ ጊዜ አሰልፈህ አንደኛው ለረጅም ጊዜ ኢትዮጵያ ውስጥ ተጫውቶ የማያውቅ ሌሎች ደግሞ ተቀምጠው የነበሩ ከመሆናቸው ጋር የጨዋታ ዝግጁነት ችግር ነበር ፤ በመከላከሉ 100% ጥሩ ነበርን ፊት ላይ ለማቀናጀት ጊዜ ይፈልጋል ከዚህ አንፃር ጥሩ ነው ማለት እችላለሁ።

በጨዋታው በሁለቱም በኩል ዒላማውን የጠበቀ ሙከራ ስላለመደረጉ

“ፊት ላይ ያመጣናቸው ልጆች አዲስ ስለሆኑ ክፍተቶች ነበሩብን የጨዋታ ዝግጁነት በአንድ ቀን የሚመጣ አይደለም ያንን እንቀበላለን።

ከጨዋታው መጀመር አንስቶ ቡድኑን ስላበረታቱት የመከላከያ ማርሽ ቡድን አባላት

“የመከላከያም ቢሆኑ ኳሱን ሊደግፉ ነው የመጡት ድሮ የነበረውን የኳስ ድባብ ለመመለስ ነው እንጂ የመጡት መከላከያን ብለው አይደለም ለብቻችን አልዘፈኑልንም ለጠቅላላ ህዝብ ነው እኔ እንደውም የምጠይቀው ሁሌም እንዲቀጥል ነው ምክንያቱም የእግርኳሱ ድባብ መምጣት አለበት ተመልካቹም እንደዚህ አይነት ኢትዮጵያ የምትወደስበት ነገር ሲፈጠር ይደሰታል ብዬ አስባለሁ።”

አሰልጣኝ መሳይ ተፈሪ – አርባምንጭ ከተማ

ሰለ ጨዋታው

“በቀጥተኛ ኳስ ከሜዳቸው ለመውጣት ጥረት ያደርጋሉ እኛም ከወትሮው በተለየ ኃላ ላይ በዛ አርገን ነበር የመጣነው የባላጋራን የጨዋታ መንገድ ታሳቢ አድርገነው ለጨዋታ የምንቀርበው ቁጥሮች እንደሚያሳዩት በምንፈልገው ልክ ባይሆን የጨዋተ ዕቅዳችን ተሳክቷል ብዬ አስባለሁ።

ዒላማውን የጠበቀ ሙከራ በጨዋታው ስላለመደረጉ

“በሁለቱም አጋማሾች ለመድረስ ሞክረናል ግን ኳሶቹ ወደ ግብ ባይደርሱም አደገኛ ሙከራዎችን አድርገናል።

የአቻ ውጤት ስለማብዛታቸው

“ከአቻዎች ባለፈ ሦስት ነጥብ ስናስመዘግብ በደንብ ነው ወደ ላይ ከፍ የምንለው በመጀመሪያው ዙር ስንጀምር በሽንፈት ነበር አሁን ግን በአንድ ነጥብ ጀምረናል እዚህ ላይ ደግም አንድ አንድ እያልክ ሦስት ነጥብ ስትጨምርበት ወደ ላይ ከፍ ማለት ይቻላል ግን አንዷንም አክብሮ መያዝ ያስፈልጋል በቀላሉ ስለማትገኝ ማለት ነው።”