ወልቂጤ ከተማ ውሳኔ ተላለፈበት

አሠልጣኝ ጻውሎስ እና ረዳታቸው እዮብ ወልቂጤ ከተማ ላይ ያቀረቡትን ቅሬታ ሲከተታተል የቆየው የዲሲፒሊን ኮሚቴ በመጨረሻም ውሳኔ አሳልፏል።

ወልቂጤ ከተማ ከወራት በፊት በአሰልጣኝ ጳውሎስ ጌታቸውን እና በረዳታቸው አሰልጣኝ እዮብ ማለ ላይ የዕግድ ውሳኔ ያሳለፈ ሲሆን ከቀናት በኋላ የታችኛውን ቡድን ዝቅ ብለው እንዲያሰለጥኑ ክለቡ መወሰኑ ይታወሳል። ይህንን ውሳኔ ተከትሎ “የስድስት ወራት ቀሪ የውል ዘመን እያለን የተወሰነው ውሳኔ ተገቢ አይደለም።” በማለት ሁለቱ አሰልጣኞች ለኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌድሬሽን የዲሲፕሊን ኮሚቴ የቅሬታ ደብዳቤያቸውን አስገብተው ነበር።

የሁለቱን አካላት ጉዳይ ሲመረምር የቆየው የዲሲፒሊን ኮሚቴ በስተመጨረሻም በወልቂጤ ከተማ ላይ ውሳኔ ማሳለፉን ሶከር ኢትዮጵያ ከህግ አማካሪው አቶ ብርሀኑ በጋሻው ያገኘችው መረጃ ይጠቁማል። በዚህም ክለቡ ሁለቱንም አሰልጣኞች በውላቸው መሠረት ወደ ስራ ገበታቸው እንዲመልስ ካልሆነ እና ማሰራት ካልፈለገ በውላቸው አንቀጽ 4 መሠረት ተፈፃሚ እንዲያደርግ እንዲሁም እስካሁን ያልተከፈላቸው ደሞዝ እንዲከፈል ተወስኗል። ክለቡ ይህ ውሳኔ በደረሰው በሰባት ቀን ውስጥ ተግባራዊ እንዲያደርግ ውሳኔውን ካልፈፀመ ደግሞ ከፌዴሬሽኑ ምንም ዓይነት ግልጋሎ እንዳያገኝ እንዲሁም ከተጫዋቾች ዝውውር እና ምዝገባ እንዲታደግ ተወስኗል። ወልቂጤ ከተማ በውሳኔው ተቃውሞ ካለው ይግባኝ የመጠየቅ መብት እንዳለውም ተጠቁሟል።